ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ መጽሐፈ ሲራክ 50 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የኦንያ ልጅ ስምዖን 1 የኦንያ ልጅ ታላቁ ካህን ስምዖንም በሕይወቱ ቤተ መቅደስን አደሰ፤ በዘመኑም ቤተ መቅደስን አጸና። 2 እንዲሁም የቅጥሩን መሠረት ዕጥፍ አድርጎ ሠራ ካህን የሚለብሰውንም ቀጭን ልብስ ሠራ። 3 በዘመኑም የውኃዎች ምንጮች አልጐደሉም፤ የጕድጓዱም ውኃ ብዛቱ እንደ ባሕር ውኃ ነበር። 4 ሕዝቡም እንዳይወድቁ ይጠነቀቅላቸው ነበር፤ ከተማዋንም ከጠላት ለመከላከል መሸገ። 5 ከቤተ መቅደስ መጋረጃ በወጣ ጊዜም በሕዝቡ መካከል ተከበረ። 6 በደመና ውስጥ እንደ አጥቢያ ኮከብና በምልዐት ቀን እንደ ሙሉ ጨረቃ ነበረ። 7 በልዑል መቅደስም ላይ እንደምታበራ ፀሐይ ነበረ። በብሩህ ደመናም ውስጥ ብርሃን እንደሚሰጥ ቀስተ ደመና ነበር። 8 እንደ መጸው ወራት ጽጌረዳም ነበር፤ በውኃ መፍሰሻ አጠገብ እንደሚያፈራ አበባም ነበር፤ በመከርም ወራት እንደ ሊባኖስ ዛፍ ቅርንጫፍ ነበር። 9 በጥና እሳት ላይ እንዳለ ነጭ ዕጣንም ነበር። ተመትቶ እንደ ተሠራ የወርቅ ዕቃም ነበር። በጌጥ ላይ እንዳለ የከበረ ዕንቍም ነበር፤ 10 ፍሬዋ ብዙ እንደ ሆነ የዘይት እንጨት፥ ከደመና በታች እንደሚያድግ የዋንዛ ዛፍ ነበር። 11 እርሱም የክብር ልብሱን በለበሰ ጊዜ፥ የመመኪያውንም ጌጥ በለበሰ ጊዜ፥ ወደ ተቀደሰውም መሠዊያ በወጣ ጊዜ፥ በቅድስና ልብሱ ተከበረ። 12 ከካህናቱም እጅ የመሥዋዕቱን ሥጋ ክፍል በተቀበለ ጊዜ፥ በመሠዊያው አጠገብ ይቆም ነበር፤ ወንድሞቹም በዙሪያው ቁመው ይጋርዱት ነበር፤ እንደ ሊባኖስ ለጋ ዝግባና እንደ ዘንባባም ዛፍ ይከቡት ነበር። 13 እንዲሁም የአሮን ልጆች ሁሉ የክብር ልብሳቸውን ለብሰው፥ የእግዚአብሔርን መባእ በእጃቸው ይዘው፥ በእስራኤል ማኅበር ሁሉ ፊት ይቆሙ ነበር። 14 በመሠዊያውም ሥራቸውን ይፈጽሙ ነበር፤ ሁሉን የሚችል የልዑልንም መሥዋዕት ያዘጋጁ ነበር። 15 የወይኑን ጽዋዕ ይዞ እጁን አነሣ፤ የወይኑን ዘለላ ደምም አፈሰሰ፤ ለንጉሠ ነገሥት ለልዑል በጎ መዓዛ አድርጎ በመሠዊያው እግር ሥር ያፈስሰው ነበር። 16 የአሮንም ልጆች እየጮሁ ምስጋናውን ይናገሩ ነበር፤ ተመትቶ የተሠራ የብር መለከትንም ይነፉ ነበር፤ በልዑልም ፊት ማሰባሰቢያ ሊሆን ቃላቸውን ያሰሙ ነበር። 17 ያን ጊዜም ሕዝቡ ሁሉ በአንድነት ያርፉ ነበር፤ በምድር ላይም በግንባራቸው ይሰግዱ ነበር፤ ሁሉን ለሚገዛ ለልዑል እግዚአብሔርም ምስጋና ያቀርቡ ነበር። 18 መዘምራኑም በቃላቸው ያመሰግኑት ነበር፥ የዜማቸውም ድምፅ ቤቱን ያስተጋባው ነበር። 19 ሕዝቡም ወደ ልዑል እግዚአብሔር ይጸልዩ ነበር፤ በእግዚአብሔር ሕግ ጸንተው ሥርዐቱን እስኪጨርሱ ድረስ ይቅር በሚል በእግዚአብሔር ፊት ይለምኑ ነበር፤ ሥርዐቱንም ያከናውኑ ነበር። 20 ከዚህም በኋላ እርሱ ወርዶ የእግዚአብሔርን በረከት በአንደበቱ ይሰጣቸው ዘንድ፥ በስሙም ይመኩ ዘንድ በእስራኤል ልጆች ማኅበር ሁሉ ላይ እጁን አነሣ። 21 የልዑልንም በረከት ይቀበሉ ዘንድ ዳግመኛ ሰገዱ። 22 አሁንም በሁሉም ቦታ ብዙ ተአምራት የሚያደርገውን፥ ከእናታችን ማኅፀን ጀምሮ ዘመናችንንም የሚያረዝመውን፥ እንደ ቸርነቱም ይቅርታውን የሚያደርግልንን፥ የሁሉን ፈጣሪ አመስግኑት። 23 የልቡና ደስታንም ይሰጠናል፤ በዘመናችንም ሰላምን ያደርጋል፤ ለእስራኤልም ለዘለዓለም። 24 በቸርነቱም ከእኛ ጋር የታመነ ነው፤ በዘመናችንም አዳነን። 25 ሰውነቴ ሁለት ወገኖችን ጠላች፤ ሦስተኛው ግን ሕዝብ አይደለም። 26 እነዚህም በሰማርያና በፍልስጥኤም ተራራ የሚኖሩ፥ በሰቂማ የሚኖሩ የአሞሬዎንም ሰዎች ናቸው። 27 ጥበብን ከልቡ ያነቃት የኢየሩሳሌም ሰው የሲራክ አልዓዛር ልጅ እኔ ኢያሱ የጥበብንና የምክርን ትምህርት በዚህ መጽሐፍ ጻፍሁ። 28 ይህን እንደዚህ የሚያደርግ፥ በዚያም የሚራቀቅ ብፁዕ ነው፤ ይህንም በልቡ የሚጠብቀው ጠቢብ ይሆናል። 29 ይህንም የሚያደርግ ሁሉን ይችላል፤ የእግዚአብሔር ብርሃን ይመራዋልና። |