Biblia Todo Logo
የመስመር ላይ መጽሐፍ ቅዱስ
- ማስታወቂያዎች -

ይህ መፅሐፍ በእግዚአብሔር አልተነፀረም እና የክርስቲያን ካኖን ወይም የአይሁድ ታናክ ክፍል አይደለም። ለታሪክና ለጥናት ዓላማ ብቻ ይታያል። ሙሉ ማብራሪያን ይመልከቱ

መጽ​ሐፈ መቃ​ብ​ያን ካልእ 6 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)

1 የእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ጠላት ትዕ​ቢ​ተ​ኛው ጺሩ​ጻ​ይ​ዳን የሐ​ሰት ካህ​ና​ት​ንና የጣ​ዖ​ታ​ቱን አገ​ል​ጋ​ዮች ሾመ።

2 መሥ​ዋ​ዕት ይሠ​ዉ​ላ​ቸው ነበር፤ ወይ​ኑ​ንም ያፈ​ስ​ሱ​ላ​ቸው ነበር።

3 እነ​ር​ሱም የሚ​በ​ሉና የሚ​ጠጡ ይመ​ስ​ለው ነበር።

4 በየ​ጧ​ቱም ላሞ​ች​ንና በጎ​ችን፥ ፍየ​ሎ​ች​ንና ጊደ​ሮ​ች​ንም ይሰ​ጣ​ቸው ነበር፤ ማታና ጧትም መሥ​ዋ​ዕት ይሠዋ ነበር፤ ከዚ​ያ​ችም ከረ​ከ​ሰ​ችው መሥ​ዋ​ዕት ይበላ ነበር።

5 ዳግ​መ​ኛም ለጣ​ዖ​ታቱ ይሠዉ ዘንድ ሌሎች ሰዎ​ችን ያነ​ሣ​ሷ​ቸ​ውና ግድ ይሏ​ቸው ነበር እንጂ እነ​ርሱ ብቻ የሚ​ያ​ደ​ር​ጉት አል​ነ​በ​ረም።

6 የመ​ቃ​ቢ​ስ​ንም ልጆች ያማሩ እንደ ሆኑና ፈጣ​ሪ​ያ​ቸው እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ርን እን​ደ​ሚ​ያ​መ​ል​ኩት ባዩ​አ​ቸው ጊዜ እን​ዲ​ሠ​ዉና ከረ​ከ​ሰ​ች​ውም መሥ​ዋ​ዕት እን​ዲ​በሉ የጣ​ዖ​ታቱ ካህ​ናት ያስ​ት​ዋ​ቸው ዘንድ ወደዱ፤ እነ​ዚህ የተ​ባ​ረኩ የመ​ቃ​ቢስ ልጆች ግን እንቢ አሏ​ቸው።

7 የአ​ባ​ታ​ቸ​ውን ትእ​ዛዝ ይጠ​ብ​ቃ​ሉና፥ በጎ ሥራ​ንም በመ​ሥ​ራት ጸን​ተ​ዋ​ልና፥ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ር​ንም ፈጽ​መው ይፈ​ሩ​ታ​ልና እነ​ር​ሱን እሺ ማሰ​ኘት ተሳ​ና​ቸው።

8 ባሰ​ሯ​ቸ​ውና በሰ​ደ​ቧ​ቸው፥ በቀ​ሟ​ቸ​ውም ጊዜ፥

9 ለጣ​ዖ​ቶ​ችም መስ​ገ​ድ​ንና መሠ​ዋ​ትን እንቢ እን​ዳሉ ለን​ጉሡ ለጺ​ሩ​ጻ​ይ​ዳን ነገ​ሩት።

10 ስለ​ዚ​ህም ንጉሡ ተቈጣ፤ አዘ​ነም፤ ያመ​ጧ​ቸ​ውም ዘንድ አዘዘ፤ አም​ጥ​ተ​ውም በፊቱ አቆ​ሙ​አ​ቸው፤ እር​ሱም “ለጣ​ዖ​ቶች ስገዱ፤ መሥ​ዋ​ዕ​ት​ንም ሠዉ” አላ​ቸው።

11 እነ​ር​ሱም መል​ሰው እን​ዲህ አሉት፥ “እኛስ በዚህ ነገር አን​መ​ል​ስ​ል​ህም፤ ለረ​ከሱ ለጣ​ዖ​ቶ​ች​ህም መሥ​ዋ​ዕ​ትን አን​ሠ​ዋም።”

12 በብዙ ሥራም አስ​ፈ​ራ​ራ​ቸው፤ ነገር ግን በእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔር አም​ነው ልባ​ቸ​ውን አስ​ጨ​ክ​ነ​ዋ​ልና አል​ቻ​ላ​ቸ​ውም።

13 እሳ​ትም አን​ድዶ ጨመ​ራ​ቸው፤ እነ​ር​ሱም ነፍ​ሳ​ቸ​ውን ለእ​ግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ሰጡ።

14 ከሞቱ በኋ​ላም ሕያ​ዋን ሆነው፥ የተ​መ​ዘዙ ሰይ​ፎ​ቻ​ቸ​ውን ይዘው በመ​ን​ግ​ሥቱ ዙፋን ተኝቶ ሳለ በሌ​ሊት ታዩት፤ እር​ሱም ፈጽሞ ፈራ።

15 እር​ሱም እን​ዲህ አላ​ቸው፥ “ጌቶች እሺ በሉኝ፤ ምን ላድ​ር​ግ​ላ​ችሁ? ያዘ​ዛ​ች​ሁ​ኝን ሁሉ አደ​ርግ ዘንድ ነፍ​ሴን አት​ው​ሰ​ዷት፤” ፈጽ​መ​ውም አስ​ፈ​ሩት።

16 እነ​ር​ሱም፥ “እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ፈጣ​ሪህ እንደ ሆነ አስብ” እያሉ የሚ​ገ​ባ​ውን ሁሉ ነገ​ሩት፤ “ከዚ​ህም ትዕ​ቢ​ትህ የሚ​ሽ​ር​ህና ከአ​ባ​ትህ ከዲ​ያ​ብ​ሎስ ጋራ ወደ ታች ወደ ገሃ​ነም የሚ​ያ​ወ​ር​ድህ አለ፤ በዚ​ያም አን​ተን የበ​ደ​ል​ንህ በደል ሳይ​ኖር፥ ፈጣ​ሪ​ያ​ችን እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ር​ንም እያ​መ​ለ​ክን ሳለን፥ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ር​ነ​ቱ​ንም በመ​ፍ​ራት እየ​ሰ​ገ​ድ​ን​ለት ሳለን በእ​ሳት እን​ዳ​ቃ​ጠ​ል​ኸን ፍዳ​ህን ሁሉ ትጨ​ር​ሳ​ለህ።

17 እርሱ ሁሉን የፈ​ጠረ ነውና፥ ሰማ​ይ​ንና ምድ​ርን፥ ባሕ​ሩ​ንና በው​ስጧ ያለ​ው​ንም ሁሉ፥

18 ፀሐ​ይ​ንና ጨረ​ቃ​ንም፥ ከዋ​ክ​ብ​ት​ንም፥ ፍጥ​ረ​ቱ​ንም ሁሉ የፈ​ጠረ እርሱ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ነውና።

19 “በላይ በሰ​ማይ፥ በታ​ችም በም​ድር ከእ​ርሱ በቀር ሌላ አም​ላክ የለም፤ ሁሉን የሚ​ችል እርሱ ነው፤ የሚ​ሳ​ነ​ውም የለም። የሚ​ገ​ድ​ልና የሚ​ያ​ድን፥ የሚ​ገ​ር​ፍና ይቅር የሚል እርሱ ነው።

20 ሰማ​ይ​ንና ምድ​ርን የሚ​ገዛ እርሱ ነውና ከእጁ የሚ​ያ​መ​ልጥ የለም።

21 ከአ​ንተ ከወ​ን​ጀ​ለ​ኛ​ውና አባ​ትህ ሰይ​ጣን ልቡ​ና​ቸ​ውን ካሳ​ወ​ራ​ቸው እንደ አንተ ከአሉ ከወ​ን​ጀ​ለ​ኞች በቀር እርሱ ከፈ​ጠ​ረው ፍጥ​ረት ከት​እ​ዛዙ የሚ​ወጣ የለም፤ አን​ተና እነ​ዚያ ጣዖ​ታ​ቶ​ች​ህም እስከ ዘለ​ዓ​ለም ድረስ መውጫ ወደ​ሌ​ለ​ባት ወደ ገሃ​ነም በአ​ን​ድ​ነት ትወ​ር​ዳ​ላ​ችሁ።

22 በእኛ ክፉ ነገ​ርን ታደ​ርግ ዘንድ ይኸን ክፉ ሥራ ያስ​ተ​ማ​ረህ መም​ህ​ርህ ሰይ​ጣን ነው እንጂ ይኸን የም​ታ​ደ​ርግ አንተ ብቻ አይ​ደ​ለ​ህ​ምና።

23 የፈ​ጠ​ረህ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔ​ር​ንም አላ​ሰ​ብ​ኸ​ውም፤ ራስ​ህ​ንም እንደ ፈጣ​ሪህ እንደ እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር ታደ​ር​ጋ​ለህ።

24 እግ​ዚ​አ​ብ​ሔር እስ​ኪ​ያ​ዋ​ር​ድህ ድረስ በእ​ጅህ ሥራና በጣ​ዖ​ቶ​ችህ ትታ​በ​ያ​ለህ፤ በም​ድር ላይም ስለ ሠራ​ኸው ኀጢ​አ​ት​ህና በደ​ልህ ሁሉ ይበ​ቀ​ል​ሃል።”

ተከተሉን:



ማስታወቂያዎች