ዘፀአት 30 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የዕጣን መሠውያ ( ዘፀ. 37፥25-28 ) 1 “የዕጣን መሠዊያውን ከማይነቅዝ ዕንጨት ሥራ። 2 ርዝመቱ አንድ ክንድ፥ ስፋቱም አንድ ክንድ፥ አራት ማዕዘን ይሁን፤ ቁመቱም ሁለት ክንድ ይሆናል፤ ቀንዶቹም ከእርሱ ይሠሩ። 3 ወለሉንና የግድግዳውንም ዙሪያ፥ ቀንዶቹንም በጥሩ ወርቅ ትለብጠዋለህ፤ በዙሪያውም የጥሩ ወርቅ ክፈፍ ታደርግለታለህ። 4 ከክፈፉም በታች ሁለት የወርቅ ቀለበቶች አድርግለት። በዚህና በዚያ በሁለቱ ጐን ታደርጋቸዋለህ፤ እርሱን ያነሡባቸው ዘንድ የመሎጊያዎቹ መግቢያ ይሁኑ። 5 መሎጊያዎቹንም ከማይነቅዝ ዕንጨት አድርግ፤ በወርቅም ለብጣቸው። 6 ለአንተ በምገለጥበት በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው መጋረጃ ፊት ታኖረዋለህ። 7 አሮንም በጎ መዓዛ ያለው የደቀቀ ዕጣን በውስጡ በየማለዳው ይጠንበት፤ መብራቶቹን ሲያዘጋጅ ይጠነው። 8 ይህም በእግዚአብሔር ፊት ለልጅ ልጃችሁ የዘወትር ዕጣን ይሆን ዘንድ አሮን በማታ ጊዜ መብራቶቹን ሲያበራ ያጥነዋል። 9 ሌላም ዕጣን፥ የሚቃጠለውንም መሥዋዕት፥ የእህሉንም ቍርባን አታቀርብበትም፤ የመጠጥም ቍርባን አታፈስስበትም። 10 አሮንም በዓመት አንድ ጊዜ በቀንዶቹ ላይ ማስተስረያ ያደርጋል፤ በዓመት አንድ ጊዜ ኀጢአትን ከሚያነጻው ደም ይወስዳል፤ የልጅ ልጆቻቸውንም እንዲያነጻ ያደርጋል፤ ይህም ለእግዚአብሔር ቅዱሰ ቅዱሳን ነው።” ቤዛ ነፍስ 11 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 12 “አንተ የእስራኤልን ልጆች ቍጥር የወሰድህ እንደ ሆነ በቈጠርሃቸው ጊዜ መቅሠፍት እንዳይሆንባቸው፥ በቈጠርሃቸው ጊዜ ከእነርሱ ሰው ሁሉ እንደ ቍጥራቸው መጠን የነፍሱን ቤዛ ለእግዚአብሔር ይስጥ። 13 ይቈጠሩ ዘንድ የሚያልፉት ሁሉ የሚሰጡት ይህ ነው፤ እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን የሰቅል ግማሽ ይሰጣል። ሰቅሉም ሃያ አቦሊ ነው፤ የሰቅሉም ግማሽ ለእግዚአብሔር ቍርባን ነው። 14 ይቈጠር ዘንድ የሚያልፈው ሁሉ፥ ከሃያ ዓመት ጀምሮ ከዚያም ከፍ ያለ፥ የእግዚአብሔርን ስጦታ ይሰጣል። 15 ለነፍሳችሁ ቤዛ የእግዚአብሔርን ስጦታ ስትሰጡ ባለ ጠጋው ከሰቅል ግማሽ አይጨምር፤ ድሃውም አያጕድል። 16 የማስተስረያውንም ገንዘብ ከእስራኤል ልጆች ወስደህ ለምስክሩ ድንኳን ማገልገያ ትሰጠዋለህ፤ በእግዚአብሔርም ፊት ለነፍሳችሁ ቤዛ እንዲሆን ለእስራኤል ልጆች መታሰቢያ ይሁን።” የመታጠቢያ ሰን 17 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 18 “የመታጠቢያ ሰን ከናስ፥ መቀመጫውንም ከናስ ሥራ፤ በምስክሩ ድንኳንና በመሠዊያው መካከል ታኖረዋለህ፤ ውኃም ትጨምርበታለህ። 19 አሮንና ልጆቹም እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን ይታጠቡበታል። 20 ወደ ምስክሩ ድንኳን በገቡ ጊዜ፥ ለእግዚአብሔርም የእሳት መሥዋዕት ያቃጥሉ ዘንድ ወደ መሠዊያው ሊያገለግሉ በቀረቡ ጊዜ እንዳይሞቱ ይታጠቡበታል። 21 ወደ ምስክሩም ድንኳን በገቡ ጊዜ እንዳይሞቱ እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን ይታጠቡ፤ ይህም ለእነርሱ ከእነርሱም በኋላ ለልጆቻቸው የዘለዓለም ሥርዐት ይሆንላቸዋል።” የቅብዐት ዘይት 22 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረው፦ 23 “አንተም ክቡሩን ሽቱ ውሰድ፤ የተመረጠ የከርቤ አበባ አምስት መቶ ሰቅል፥ የዚህም ግማሽ ጣፋጭ ቀረፋ ሁለት መቶ አምሳ ሰቅል፤ ያማረ የጠጅ ሣርም እንዲሁ ሁለት መቶ አምሳ ሰቅል፤ 24 ብርጉድም አምስት መቶ ሰቅል እንደ መቅደሱ ሰቅል ሚዛን፥ የወይራ ዘይትም አንድ የኢን መስፈሪያ ትወስዳለህ። 25 በቀማሚም ብልሃት እንደ ተሠራ ቅመም፥ የተቀደሰ የቅብዐት ዘይት ታደርገዋለህ፤ የተቀደሰ የቅብዐት ዘይት ይሆናል። 26 የምስክሩንም ድንኳን፥ የምስክሩንም ታቦት፥ 27 ገበታውንም፥ ዕቃውንም ሁሉ፥ መቅረዙንም፥ ዕቃውንም፥ የዕጣን መሠዊያውንም፥ 28 ለሚቃጠል መሥዋዕት የሚሆነውን መሠዊያና ዕቃውንም ሁሉ፥ የመታጠቢያውን ሰንና መቀመጫውንም ትቀባበታለህ። 29 ሁሉንም ትቀድሳቸዋለህ፤ ቅዱሰ ቅዱሳንም ይሆናሉ፤ የሚነካቸውም ሁሉ ቅዱስ ይሆናል። 30 በክህነትም ያገለግሉኝ ዘንድ አሮንንና ልጆቹን ቅባቸው፤ ቀድሳቸውም። 31 አንተም ለእስራኤል ልጆች እንዲህ ብለህ ተናገር፤ ይህ ለልጅ ልጃችሁ የተቀደሰ የቅብዐት ዘይት ይሁን። 32 በሌላ ሰው ሥጋ ላይ አይፍሰስ፤ እንደ እርሱም የተሠራ ሌላ ቅብዐት አታድርጉ፤ ቅዱስ ነው፤ ለእናንተም ቅዱስ ይሁን። 33 እንደ እርሱ ያለውን የሚያደርግ ሰው፥ በሌላም ሰው ላይ የሚያፈስሰው ከሕዝቡ ተለይቶ ይጥፋ።” የዕጣን ዝግጅት 34 እግዚአብሔርም ሙሴን አለው፥ “ጣፋጭ ሽቱ ውሰድ፤ የሚንጠባጠብ ሙጫ፥ በዛጎል ውስጥ የሚገኝ ሽቱ፥ የሚሸትትም ሙጫ፥ ጥሩም ዕጣን ውሰድ፤ የሁሉም መጠን ትክክል ይሁን። 35 በቀማሚ ብልሃት እንደ ተሠራ፥ የተቀመመ ንጹሕና ቅዱስ ዕጣን አድርገው። 36 ከእርሱም ጥቂት ትወቅጣለህ፤ ታልመውማለህ፤ ከዚያም ለአንተ በምገለጥበት በምስክሩ ድንኳን ውስጥ በምስክሩ ፊት ታኖረዋለህ። እርሱም ቅዱሰ ቅዱሳን ይሁንላችሁ። 37 በዚህም አሠራር የዚህን ዕጣን ዐይነት ለእናንተ አታድርጉ፤ በእናንተም ዘንድ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ይሁን። 38 ሊያሸትተውም እንደ እርሱ የሚያደርግ ሰው ከሕዝቡ ተለይቶ ይጥፋ።” |