አንኩስ ዳዊትን ወደ ሴቄላቅ እንደ መለሰው1 ፍልስጥኤማውያንም ጭፍሮቻቸውን ሁሉ ወደ አፌቅ ሰበሰቡ፤ እስራኤላውያንም በኢይዝራኤል ባለው ውኃ ምንጭ አጠገብ ሰፈሩ። 2 የፍልስጥኤማውያንም አለቆች በመቶ በመቶ፥ በሺህ በሺህ እየሆኑ ያልፉ ነበር፤ ዳዊትና ሰዎቹም ከአንኩስ ጋር በኋለኛው ጭፍራ በኩል ያልፉ ነበር። 3 የፍልስጥኤማውያን አለቆች፥ “እነዚህ በኋላ የሚሄዱት እነማን ናቸው?” አሉ፤ አንኩስም የፍልስጥኤማውያንን አለቆች፥ “ይህ የእስራኤል ንጉሥ የሳኦል አገልጋይ ዳዊት ነው፤ እርሱ በእነዚህ ሁለት ዓመታት ከእኛ ጋር ነበረ፤ ወደ እኔም ከተጠጋበት ቀን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ምንም አላገኘሁበትም” አላቸው። 4 የፍልስጥኤማውያን አለቆች ግን በእርሱ ላይ ተቈጥተው፥ “ይህን ሰው ወደ አመጣህበት ቦታ መልሰው፤ በሰልፉም ውስጥ ጠላት እንዳይሆነን ከእኛ ጋር ወደ ሰልፍ አይውረድ፤ ከጌታው ጋር በምን ይታረቃል? የእነዚህን ሰዎች ራስ በመቍረጥ አይደለምን? 5 ወይስ ሴቶች፦ ‘ሳኦል ሺህ ገደለ፥ ዳዊት ዐሥር ሺህ ገደለ’ ብለው በዘፈን የዘመሩለት ይህ ዳዊት አይደለምን?” አሉት። 6 አንኩስም ዳዊትን ጠርቶ፥ “ሕያው እግዚአብሔርን! አንተ በፊቴ ጻድቅና ደግ ነህ፤ ከእኔም ጋር በጭፍራው በኩል መውጣትህና መግባትህ በፊቴ መልካም ነው፤ ወደ እኔ ከመጣህ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ አንዳች ክፋት አላገኘሁብህም፤ ነገር ግን በአለቆች ዘንድ አልተወደድህም። 7 አሁንም ተመልሰህ በሰላም ሂድ፤ በፍልስጥኤማውያንም አለቆች ዐይን ክፋት አታድርግ” አለው። 8 ዳዊትም አንኩስን፥ “ምን አድርጌአለሁ? ሄጄስ ከጌታዬ ከንጉሡ ጠላቶች ጋር እንዳልዋጋ፥ በፊትህ ከተቀመጥሁ ጀምሬ እስከ ዛሬ ድረስ በእኔ በአገልጋይህ ምን በደል አግኝተህብኛል?” አለው። 9 አንኩስም መልሶ ዳዊትን፥ “በዐይኔ ፊት ጻድቅ እንደ ሆንህ አውቃለሁ፤ ነገር ግን የፍልስጥኤማውያን አለቆች፦ ‘ከእኛ ጋር ወደ ሰልፍ አይወጣም’ አሉ። 10 አሁንም አንተ ከአንተም ጋር የመጡ የጌታህ ብላቴኖች ማልዳችሁ ተነሡ፤ ሲነጋም ተነሥታችሁ ወደ መጣችሁበት ሂዱ። ክፉ ነገርንም በልብህ አታኑር፤ በዐይኔ ፊት ጻድቅ ነህና፥ በነጋም ጊዜ ገሥግሣችሁ መንገዳችሁን ሂዱ” አለው። እነርሱም ሄዱ። 11 ዳዊትና ሰዎቹም ማልደው ይሄዱ ዘንድ፥ ወደ ፍልስጥኤማውያንም ሀገር ይመለሱ ዘንድ ተነሡ። ፍልስጥኤማውያንም ሊዋጉ ወደ ኢይዝራኤል ወጡ። |