ኤርምያስ 46 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ግብፅ በከርከሚሽ ላይ ድል እንደ ሆነች 1 በአሕዛብ ላይ ወደ ነቢዩ ወደ ኤርምያስ የመጣው የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው። 2 በግብፅ ላይ፤ በኤፍራጥስ ወንዝ አጠገብ በከርኬማስ በነበረው፥ በይሁዳ ንጉሥ በኢዮስያስ ልጅ በኢዮአቄም በአራተኛው ዓመተ መንግሥት የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር በመታው በግብፅ ንጉሥ በፈርዖን ኒካዑ ሠራዊት፥ 3 “ጋሻና ጦር ያዙ፤ ወደ ሰልፍም ቅረቡ። 4 ፈረሰኞች ሆይ፥ ፈረሶችን ጫኑና ውጡ፤ ራስ ቍርንም ደፍታችሁ ቁሙ፤ ጦርንም ሰንግሉ፤ ጥሩርንም ልበሱ። 5 ፈርተው ወደ ኋላ ሲመለሱ፥ ኀያላኖቻቸውም ሲደክሙ፥ ወደ ኋላቸውም ሳይመለከቱ ፈጥነው ሲሸሹ ለምን አየሁ? በዙሪያቸውም ይከቡአቸዋል፥” ይላል እግዚአብሔር። 6 ፈጣኑም አያመልጥም፤ ኀያሉም አይድንም፤ በሰሜን በኤፍራጥስ ወንዝ በኩል ደክመው ወደቁ። 7 ይህ እንደ ወንዝ የሚነሣ ውኃውም እንደ ወንዝ የሚናወጥ ማን ነው? 8 ግብፅ እንደ ወንዝ ይነሣል፤ ከባሕሩም እንደሚታወክ ማዕበል ይሆናል፤ እርሱም እንዲህ ብሏል፥ “እነሣለሁ፤ ምድርንም ሁሉ እከድናለሁ፤ ከተሞችንና የሚኖሩባቸውን አጠፋለሁ። 9 በፈረሶች ተቀመጡ፤ ሰረገሎችንም አዘጋጁና ውጡ፤ ጋሻም የሚያነግቡ የኢትዮጵያና የሊብያ ኀያላን፥ ቀስትንም ይዘው የሚስቡ የሉድ ኀያላን ይውጡ። 10 ያ ቀን ጠላቶቹን የሚበቀልበት የአምላካችን የእግዚአብሔር የበቀል ቀን ነው፤ የእግዚአብሔር ሰይፍ በልቶ ይጠግባል፤ በደማቸውም ይሰክራል፤ የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር መሥዋዕት በሰሜን ምድር በኤፍራጥስ ወንዝ አጠገብ ነውና። 11 ድንግሊቱ የግብፅ ልጅ ሆይ! ወደ ገለዓድ ውጪ፤ የሚቀባ መድኀኒትንም ውሰጂ፤ ለምንም የማይጠቅምሽን መድኀኒት በከንቱ አብዝተሻል። 12 ጦረኞች በጦረኞች ላይ ተሰናክለው ሁለቱ በአንድነት ወድቀዋልና አሕዛብ ቃልሽን ሰምተዋል፤ ልቅሶሽም ምድርን ሞልቶአታል።” ናቡከደነፆር ወደ ግብፅ እንደ መጣ 13 የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር እንደሚመጣና የግብፅን ምድር እንደሚመታ እግዚአብሔር ለነቢዩ ለኤርምያስ የተናገረው ቃል ይህ ነው። 14 “በግብፅ ተናገሩ፤ በሚግዶልም አውሩ፤ በሜምፎስና በጣፍናስ አሰሙ፤ ሰይፍ በዙሪያህ ያለውን በልቶአልና፦ ተነሥ ተዘጋጅም በሉ። 15 ኀይለኞችህ ስለ ምን ታጡ? እግዚአብሔር ስላደከማቸው የሉም። 16 ብዛታቸውም ደከመ፤ ወደቀም፤ አንዱም አንዱ ለጓደኛው፦ ተነሥ፤ ከአረማውያን ሰይፍ ፊት ወደ ወገናችን ወደ ተወለድንባት ምድር እንመለስ አለው። 17 በዚያም የግብፅ ንጉሥ የፈርዖንን ስም ጊዜውን የሚያሳልፍ ብለው ጠሩት። 18 እኔ ሕያው ነኝና በተራሮች መካከል እንዳለ እንደ አጤቤርዮን፥ በባሕርም አጠገብ እንዳለ እንደ ቀርሜሎስ፥ እንዲሁ በእውነት ይመጣል፥ ይላል ስሙ የሠራዊት ጌታ የሆነ ንጉሥ እግዚአብሔር። 19 አንቺ በግብፅ የምትቀመጪ ልጅ ሆይ! ሜምፎስ ባድማ ትሆናለችና፥ የሚቀመጥባትም አይገኝምና ለፍልሰት የሚሆን ዕቃ አዘጋጂ። 20 “ግብፅ የተዋበች ጊደር ናት፤ ጥፋት ግን ከሰሜን በኩል ይመጣባታል። 21 በእርስዋም ያሉ የተቀጠሩ ሠራተኞች በእርስዋ ተቀልበው እንደ ሰቡ ወይፈኖች ናቸው፤ የጥፋታቸው ቀንና የቅጣታቸው ጊዜ መጥቶባቸዋልና ተመለሱ፤ በአንድነትም ሸሹ፤ አልቆሙምም። 22 ሠራዊትም በኀይል ይዘምቱባታልና፥ እንደ እንጨት ቈራጮችም በምሳር ይመጡባታልና ድምፅዋ እንደምትሸሽ እባብ ይተማል። 23 ሊቈጠሩ የማይችሉ የዱርዋን ዛፎች ይቈርጣሉ፥ ይላል እግዚአብሔር፤ ከአንበጣ ይልቅ በዝተዋልና፥ ቍጥርም የላቸውምና። 24 የግብፅ ልጅ ታፍራለች፤ በሰሜን ሕዝብ እጅም አልፋ ትሰጣለች።” 25 የእስራኤል አምላክ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ “እነሆ የኖእ አሞንን፥ ፈርዖንንም፥ ግብጽንም፥ አማልክቶችዋንና ነገሥታቶችዋንም፥ ፈርዖንንና በእርሱም የሚታመኑትን እቀጣለሁ። 26 ነፍሳቸውንም በሚፈልጉ ሰዎች እጅ፥ በባቢሎንም ንጉሥ በናቡከደነፆር እጅ፥ በአገልጋዮቹም እጅ አሳልፌ እሰጣቸዋለሁ፤ ከዚያም በኋላ እንደ ቀድሞው ዘመን የሰው መኖሪያ ትሆናለች፥ ይላል እግዚአብሔር።” እግዚአብሔር ሕዝቡን እንደሚታደግ 27 “ነገር ግን አንተ ባሪያዬ ያዕቆብ ሆይ! አትፍራ፥ አንተም እስራኤል ሆይ! አትደንግጥ፤ እነሆ አንተን ከሩቅ፥ ዘርህንም ከተማረኩባት ምድር አድናለሁ፤ ያዕቆብም ተመልሶ ያርፋል፤ ተዘልሎም ይተኛል፤ ማንም አያስፈራውም። 28 አንተ ባሪያዬ ያዕቆብ ሆይ! እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ፥” ይላል እግዚአብሔር፤ አንተንም ያሳደድሁባቸውን አሕዛብን ሁሉ ፈጽሜ አጠፋለሁና፥ አንተን ግን ፈጽሜ አላጠፋህም፤ በመጠን እቀጣሃለሁ፥ ያለ ቅጣትም አልተውህም።” |