ኢሳይያስ 34 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)በአሕዛብ ላይ ስለሚመጣው ፍርድ 1 እናንተ አሕዛብ ሆይ፥ ቅረቡ፤ እናንተም አለቆች ሆይ፥ አድምጡ፤ ምድርና በውስጥዋም ያሉ፥ ዓለምና በውስጥዋም ያሉ ሕዝብ ሁሉ ይስሙ። 2 የእግዚአብሔር ቍጣ በአሕዛብ ሁሉ ላይ ነውና፤ መቅሠፍቱም ያጠፋቸውና ለጦር ይሰጣቸው ዘንድ በቍጥራቸው ልክ ነው። 3 ከእነርሱም የተገደሉት በድናቸው ይጣላል፤ የሬሳቸውም ግማት ይሸታል፤ ተራሮቹም ከደማቸው የተነሣ ይርሳሉ። 4 ሰማያት እንደ መጽሐፍ ጥቅልል ይጠቀለላሉ፤ ከወይንና ከበለስም ቅጠል እንደሚረግፍ ከዋክብት ሁሉ ይረግፋሉ። 5 ሰይፌ በሰማይ ሆና ሰከረች፤ እነሆ፥ በኤዶምያስና በሚጠፉት ሕዝብ ላይ ለፍርድ ትወርዳለች። 6 እግዚአብሔር መሥዋዕት በባሶራ፥ ታላቅም እርድ በኤዶምያስ ምድር አለውና የእግዚአብሔር ሰይፍ በደም ተሞልታለች፤ በበግ ስብ፥ በፍየል ደምም፥ በአውራም በግ ስብ ወፍራለች። 7 ኀያላን ከእነርሱ ጋር፥ ወይፈኖችም ከኮርማዎች ጋር ይወድቃሉ፤ ምድራቸውም በደም ትሰክራለች፤ በስባቸውም ትወፍራለች። 8 የእግዚአብሔር የፍርዱ ቀን፥ ስለ ጽዮንም ፍርድ የብድራት ዓመት ነውና። 9 ሸለቆዎችዋ ዝፍት ሆነው ይወጣሉ፤ አፈርዋም ዲን ይሆናል፤ መሬቷም በቀንና በሌሊት እንደ ዝፍት ይቃጠላል፤ ለዘለዓለምም አይጠፋም፤ 10 ጢሱም ወደላይ ይወጣል፤ ከትውልድ እስከ ትውልድም ድረስ ባድማ ሆና ትኖራለች፤ ለብዙ ዘመናትም ትጠፋለች። 11 ጭልፊቶችና ጃርት፥ ጕጕትና ቍራም ይኖሩባታል፤ መሠረቷንም በመፍረስ ገመድ ይለካሉ። አጋንንትም ያድሩባታል፤ 12 አለቆችዋ ያልቃሉ፤ ነገሥታቷና መሳፍንቷ ይጠፋሉ። 13 በከተማዎችዋም እሾህ፥ በቅጥሮችዋም አሜከላ ይበቅሉባታል፤ የአጋንንት ማደሪያና የሰጎን ስፍራ ትሆናለች። 14 በዚያም አጋንንትና ጂኖች ይገናኛሉ፤ እነርሱም እርስ በርሳቸው ይጠራራሉ፤ ጂኖችም በዚያ ይኖራሉ፤ ለራሳቸውም ማረፊያን ያገኛሉ። 15 በዚያ ጃርቶች ይዋለዳሉ፤ ምድርም ልጆችዋን በኀይል ታድናለች፤ ዋሊያዎች በዚያ ይገናኛሉ፤ ፊት ለፊትም ይተያያሉ። 16 በየቍጥራቸው ያልፋሉ፤ ከእነርሱም አንዱ አይጠፋም፤ እርስ በርሳቸው አይተጣጡም፤ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር አዝዞአቸዋልና መንፈሱም ሰብስቦአቸዋልና። 17 እርሱም ዕጣ ጣለባቸው፤ እጁም ከፈለችላቸው፤ ለዘለዓለም ይሰማሩባታል፤ ከትውልድም እስከ ትውልድ ድረስ ይወርሱአታል፤ በውስጥዋም ያርፉባታል። |