Biblia Todo Logo
La Biblia Online
- Anuncios -


መዝሙር 49 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉም


በሀብት የመተማመን ሞኝነት

1 ሕዝቦች ሁሉ ይህን ስሙ! በዓለም የምትኖሩ ሁሉ ይህን አድምጡ!

2 ከፍተኞችና ዝቅተኞች፥ ሀብታሞችና ድኾች ስሙ፤

3 አንደበቴ የጥበብ ቃላትን ይናገራል፤ የልቤ ሐሳብም ማስተዋልን ያስገኛል።

4 ሐሳቤን ወደ ምሳሌዎች አዘነብላለሁ፤ የምሳሌዎችንም ትርጒም በገና በመደርደር እገልጣለሁ።

5 ክፉ ቀን ሲመጣና ክፉዎች አታላዮች ሲከቡኝ ለምን እፈራለሁ?

6 እንዲሁም በሀብታቸው ብዛት የሚተማመኑና በብልጽግናቸው ብዛት የሚመኩ ክፉ ሰዎች ቢከቡኝስ ለምን እፈራለሁ?

7 ሰው ራሱን መቤዠትም ሆነ ለሕይወቱ ቤዛ የሚሆነውን ዋጋ ለእግዚአብሔር መክፈል አይችልም።

8 ለሰው ሕይወት የሚከፈለው ዋጋ እጅግ ብዙ ነው፤ የቱንም ያኽል ቢከፈል በቂ አይሆንም።

9 እንዳይሞትና ወደ መቃብር እንዳይወርድ፥ ለዘለዓለም እንዲኖር ለማድረግ የቱንም ያኽል ቢከፈል በቂ አይሆንም።

10 ማንም እንደሚያውቀው ጠቢባን እንኳ ከሞኞችና ከሰነፎች እኩል ይሞታሉ፤ ሁሉም ሀብታቸውን ትተው ይሄዳሉ።

11 ብዙ መሬት በየስማቸው የነበራቸው ቢሆንም እንኳ መቃብር የዘለዓለም ቤታቸውና መኖሪያቸው ነው።

12 ሰው ምንም ሀብታም ቢሆን ዘለቄታ የለውም፤ እንደ እንስሶች ይሞታል።

13 ይህ በራሳቸው የሚተማመኑ የሞኞችና የእነርሱን አባባል የሚቀበሉ ሰዎች ዕድል ፈንታ ነው።

14 እነዚህ እንደ በጎች እንዲሞቱና እንዲቀበሩ ይደረጋሉ፤ እረኛ በጎችን እንደሚመራ ሞትም እነዚህን ወደ መቃብር ይመራል፤ ትክክለኞች ሰዎች በማለዳ በመቃብራቸው ላይ ይመላለሳሉ፤ ሥጋቸውም በመቃብር ውስጥ ይበሰብሳል፤ የሙታን ዓለምም መኖሪያቸው ይሆናል። ደጋግ ሰዎችም በማለዳ ተነሥተው በእነርሱ ላይ ሥልጣናቸውን ያሳያሉ።

15 እግዚአብሔር ግን ሕይወቴን በመታደግ ከሲኦል ኀይልም አውጥቶ ወደ እርሱ ይወስደኛል።

16 ሰው ሀብታም ሲሆን፥ የቤቱም ብልጽግና እየበዛ ሲሄድ አትፍራው፤

17 በሚሞትበት ጊዜ ምንም ነገር አይወስድም፤ ሀብቱም ከእርሱ ጋር ወደ መቃብር አይወርድም።

18 ሰው በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ቢደሰትና ሁሉም ነገር ስለ ተሳካለት ቢመሰገንም እንኳ

19 በሞት ተለይቶ ዳግመኛ ብርሃንን ወደማያይበት ወደ ቀድሞ አባቶቹ ይሄዳል።

20 ያለ ማስተዋል ሀብት ያካበተ ሰው እንደ እንስሳ መሞቱ አይቀርም።

© The Bible Society of Ethiopia, 2005

© የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር፥ 1997

Bible Society of Ethiopia
Síguenos en:



Anuncios


¡Síguenos en WhatsApp! Síguenos