La Biblia Online

Anuncios

Toda la Biblia A.T. N.T.


ሆሴዕ 6 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ) መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)
ሆሴዕ 6

የንስሐ ጥሪ

1 እንዲህም ይላሉ፦ “ኑ፥ ወደ ጌታ እንመለስ፤ እርሱ ሰብሮናልና፥ እርሱም ይፈውሰናል፤ እርሱ መትቶናል፥ እርሱም ይጠግነናል።

2 ከሁለት ቀን በኋላ ነፍስ ይዘራብናል፤ በሦስተኛውም ቀን ያስነሣናል፥ በፊቱም በሕይወት ያኖረናል።

3 እኛም እንወቅ፤ ጌታን ለማወቅ እንትጋ፤ እንደ ንጋትም መገለጡ እርግጥ ነው፤ እንደ ዝናብ ምድርንም እንደሚያጠጣ እንደ በልግ ዝናብ ወደ እኛ ይመጣል።”

የእስራኤልና የይሁዳ አለመጸጸት

4 ፍቅራችሁ እንደ ማለዳ ደመና፥ በማለዳም እንደሚያልፍ ጠል ነውና ኤፍሬም ሆይ! ምን ላድርግልህ? ይሁዳ ሆይ! ምን ላድርግልህ?

5 ስለዚህ በነቢያት እጅ ቆረጥኋቸው፥ በአፌም ቃላት ገደልኋቸው፤ ፍርዴም እንደ ብርሃን ይወጣል።

6 ከመሥዋዕት ይልቅ ጽኑ ፍቅርን፥ ከሚቃጠልም መሥዋዕት ይልቅ እግዚአብሔርን ማወቅ እወዳለሁና።

7 እነርሱ ግን በአዳም ቃል ኪዳንን ተላልፈዋል፤ በዚያም ቦታ እኔን አታለውኛል።

8 ገለዓድ በደም የተቀባች የክፉ አድራጊዎች ከተማ ነች።

9 በሰው ላይ እንደሚያደቡ ወንበዴዎች እንዲሁ ካህናት አብረው ተሰበሰቡ፥ ወደ ሴኬም በሚወስደው መንገድ ላይ ይገድላሉ፤ በእርግጥም፥ ሴሰኝነትንም ያደርጋሉ።

10 በእስራኤል ቤት የሚያስፈራን ነገር አይቻለሁ፤ በዚያ የኤፍሬም ዝሙት አለ፥ እስራኤልም ረክሶአል።

11 ይሁዳ ሆይ! የሕዝቤን ምርኮ በምመልስበት ጊዜ ለአንተ ደግሞ መከር ተወስኖልሃል።

Mostrar Biblia Interlineal