ዘፀአት 16 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)መናና ድርጭት እንደ ወረደላቸው 1 የእስራኤልም ልጆች ማኅበር ሁሉ ከኤሎም ተጓዙ፤ ከግብፅ ሀገር ከወጡ በኋላ በሁለተኛው ወር ከወሩም በዐሥራ አምስተኛው ቀን በኤሎምና በሲና መካከል ወዳለችው ወደ ሲን ምድረ በዳ መጡ። 2 የእስራኤልም ልጆች ማኅበር ሁሉ በሙሴና በአሮን ላይ አንጐራጐሩ። 3 የእስራኤልም ልጆች አሉአቸው፥ “በሥጋው ምንቸት አጠገብ ተቀምጠን እስክንጠግብ ድረስ እንጀራና ሥጋ በምንበላበት ጊዜ በግብፅ ምድር በእግዚአብሔር እጅ ምነው በሞትን! ይህን ጉባኤ ሁሉ በራብ ልትገድሉ እኛን ወደዚች ምድረ በዳ አምጥታችኋልና።” 4 እግዚአብሔርም ሙሴን፥ “በሕጌ ይሄዱ ወይም አይሄዱ እንደ ሆነ እኔ እንድፈትናቸው፥ እነሆ፥ ከሰማይ እንጀራን አዘንብላችኋለሁ፤ ሕዝቡም ወጥተው ለዕለት ለዕለት የሚበቃቸውን ይሰብስቡ። 5 እንዲህም ይሆናል፤ በስድስተኛው ቀን ያመጡትን ያዘጋጁ፤ ዕለት ዕለትም ከሚለቅሙት ይልቅ ሁለት እጥፍ ይሁን” አለው። 6 ሙሴና አሮንም ለእስራኤል ልጆች ሁሉ፥ “እግዚአብሔር ከግብፅ ምድር እንደ አወጣችሁ ማታ ታውቃላችሁ፤ 7 የእግዚአብሔርንም ክብር ጥዋት ታያላችሁ፤ በእግዚአብሔር ላይ ያንጐራጐራችሁትን ሰምቶአልና፤ በእኛም ላይ የምታንጐራጕሩ እኛ ምንድን ነን?” አሉ። 8 ሙሴም፥ “እግዚአብሔር ያንጐራጐራችሁበትን ማንጐራጐራችሁን ሰምቶአልና በመሸ ጊዜ ትበሉ ዘንድ ሥጋን፥ በማለዳም ትጠግቡ ዘንድ እንጀራን እግዚአብሔር ይሰጣችኋል፤ እኛም ምንድን ነን? ማንጐራጐራችሁ በእግዚአብሔር ላይ ነው እንጂ በእኛ ላይ አይደለም” አለ። 9 ሙሴም አሮንን፥ “ለእስራኤል ልጆች ማኅበር ሁሉ፦ ‘ማንጐራጐራችሁን ሰምቶአልና ወደ እግዚአብሔር ፊት ቅረቡ’ በል” አለው። 10 አሮንም ለእስራኤል ልጆች ማኅበር ሁሉ በተናገረ ጊዜ ወደ ምድረ በዳ ፊታቸውን አቀኑ፤ እነሆም፥ የእግዚአብሔር ክብር በደመናው ታየ። 11 እግዚአብሔርም ሙሴን አለው፦ 12 “የእስራኤልን ልጆች ማንጐራጐር ሰማሁ፦ ማታ ሥጋን ትበላላችሁ፤ ማለዳም እንጀራን ትጠግባላችሁ፤ እኔም እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ በላቸው።” 13 እንዲህም ሆነ፤ በመሸ ጊዜ ድርጭቶች መጡ፤ ሰፈሩንም ሸፈኑት፤ በማለዳም በሰፈሩ ዙሪያ ጠል ወድቆ ነበር። 14 የወደቀው ጠል በአለፈ ጊዜ፥ እነሆ፥ በመሬት ላይ እንደ ውርጭ ነጭ ሆኖ ድንብላል የሚመስል ደቃቅ ነገር በምድረ በዳ ታየ። 15 የእስራኤልም ልጆች በአዩት ጊዜ እርስ በርሳቸው፥ “ይህ ምንድን ነው?” ተባባሉ። ያ ምን እንደሆነ አላወቁምና። ሙሴም አላቸው፥ “ትበሉ ዘንድ እግዚአብሔር የሰጣችሁ እንጀራ ይህ ነው። 16 ታደርጉት ዘንድ እግዚአብሔር ያዘዘው ነገር ይህ ነው፦ እያንዳንዱ ሰው ለቤተ ሰቡ ለእያንዳንዱ አንድ ጎሞር ይሰብስብ፤ እንደ ቤተ ሰቡ ቍጥር ለእያንዳንዱ በድንኳኑ አብረውት ከሚኖሩት ጋር ይሰብስብ።” 17 የእስራኤልም ልጆች እንዲሁ አደረጉ፤ አንዱ አብዝቶ፥ አንዱም አሳንሶ ሰበሰበ። 18 በጎሞርም በሰፈሩት ጊዜ እጅግ ለሰበሰበ አልተረፈውም፤ ጥቂትም ለሰበሰበ አልጐደለበትም፤ ሁሉም እያንዳንዱ ሰው ለየቤቱ ሰበሰበ። 19 ሙሴም፥ “የእስራኤልን ልጆች ማንም ከእርሱ አንዳች ለነገ አያስቀር” አላቸው። 20 ነገር ግን ሙሴን አልሰሙትም፤ አንዳንድ ሰዎችም ከእርሱ ለነገ አስቀሩ፤ እርሱም ተላ፤ ሸተተም፤ ሙሴም ተቈጣቸው። 21 ሰውም ሁሉ ለየራሱ ጥዋት ጥዋት ሰበሰበ፤ ፀሐይም በተኰሰ ጊዜ ቀለጠ። 22 እንዲህም ሆነ፤ በስድስተኛው ቀን ሁለት እጥፍ አድርገው እያንዳንዳቸው ሁለት ጎሞር እንጀራ ሰበሰቡ፤ የማኅበሩም አለቆች ሁሉ መጥተው ለሙሴ ነገሩት። 23 ሙሴም፥ “እግዚአብሔር የተናገረው ይህ ነው፦ ነገ ዕረፍት፥ ለእግዚአብሔርም የተቀደሰ ሰንበት ነው፤ ነገ የምትጋግሩትን ዛሬ ጋግሩ፤ የምትቀቅሉትንም ቀቅሉ፤ የተረፈውንም ሁሉ ለነገ እንዲጠበቅ አኑሩ” አላቸው። 24 ሙሴም እንደ አዘዘ ለነገ አኖሩት፤ አልሸተተም፤ ትልም አልሆነበትም። 25 ሙሴም፥ “የእግዚአብሔር ሰንበት ዛሬ ነውና ብሉት፤ ዛሬ በሜዳ አታገኙትም። 26 ስድስት ቀን ልቀሙት፤ ሰባተኛው ቀን ግን ሰንበት ነው፤ በእርሱ አይገኝም” አለ። 27 በሰባተኛውም ቀን እንዲህ ሆነ፤ ከሕዝቡ አንዳንድ ሰዎች ሊለቅሙ ወጡ፤ ግን ምንም አላገኙም። 28 እግዚአብሔርም ሙሴን፥ “ትእዛዞችንና ሕጎችን ለመስማት እስከ መቼ እንቢ ትላላችሁ? 29 እግዚአብሔር ሰንበትን እንደ ሰጣችሁ እዩ፤ ስለዚህ በስድስተኛው ቀን የሁለት ቀን እንጀራ ሰጣችሁ፤ ሰው ሁሉ በቤቱ ይቀመጥ፤ በሰባተኛውም ቀን ማንም ከቤቱ አይሂድ” አለው። 30 ሕዝቡም በሰባተኛው ቀን ዐረፈ። 31 የእስራኤልም ልጆች ስሙን መና ብለው ጠሩት፤ እርሱም እንደ ድንብላል ዘር ነጭ ነው፤ ጣዕሙም እንደ ማር እንጀራ ነው። 32 ሙሴም፥ “እግዚአብሔር ያዘዘው ነገር ይህ ነው፦ ከግብፅ ምድር በአወጣኋችሁ ጊዜ በምድረ በዳ ያበላኋችሁን እንጀራ ያዩ ዘንድ ከእርሱ አንድ ጎሞር ሙሉ ለልጅ ልጆቻችሁ ይጠበቅ” አለ። 33 ሙሴም አሮንን፥ “አንድ የወርቅ መሶብ ወስደህ ጎሞር ሙሉ መና አግባበት፤ ለልጅ ልጃችሁም ይጠበቅ ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት አኑረው” አለው። 34 እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው እንዲሁ ይጠበቅ ዘንድ አሮን በምስክሩ ፊት አኖረው። 35 የእስራኤልም ልጆች ወደሚኖሩባት ምድር እስከሚመጡ ድረስ አርባ ዓመት መና በሉ። 36 ወደ ፊኒቆንም ምድር እስኪመጡ ድረስ መና በሉ። ጎሞርም የሦስት ላዳን መስፈሪያ ዐሥረኛ ክፍል ነው። |