2 ዜና መዋዕል 2 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ቤተ መቅደስን ለመሥራት የተደረገ ዝግጅት ( 1ነገ. 5፥1-18 ) 1 ሰሎሞንም ለእግዚአብሔር ስም ቤት፥ ለራሱም ቤተ መንግሥት ልሥራ አለ። 2 ሰሎሞንም የሚሸከሙትን ሰባ ሺህ፥ ከተራሮችም ድንጋዮችን የሚጠርቡትን ሰማንያ ሺህ፥ በእነርሱም ላይ የተሾሙትን ሦስት ሺህ ስድስት መቶ ሰዎች ሰበሰበ። 3 ሰሎሞንም እንዲህ ሲል ወደ ጢሮስ ንጉሥ ወደ ኪራም ላከ፥ “ከአባቴ ከዳዊት ጋር እንዳደረግህ፥ የሚቀመጥበትንም ቤት ይሠራ ዘንድ የዝግባ እንጨት እንደ ላክህለት፥ እንዲሁ ለእኔ አድርግ። 4 እነሆ፥ ለእስራኤል ለዘለዓለም እንደ ታዘዘው በእግዚአብሔር ፊት የጣፋጩን ሽቱ ዕጣን ለማጠን፥ የገጹንም ኅብስት ለማኖር፥ የሚቃጠለውንም መሥዋዕት በጥዋትና በማታ፥ በሰንበታቱም፥ በመባቻዎቹም፥ በአምላካችንም በእግዚአብሔር በዓላት ለማቅረብ እኔ ልጁ ለአምላኬ ለእግዚአብሔር ስም ቤት እሠራለሁ፤ እርሱንም እቀድሳለሁ። 5 አምላካችን እግዚአብሔርም ከአማልክት ሁሉ ይልቅ ታላቅ ነውና የምሠራው ቤት ታላቅ ነው። 6 ነገር ግን ሰማይና ከሰማያት በላይ ያለ ሰማይ ክብሩን ይሸከም ዘንድ አይችልምና ለእርሱ ቤት ይሠራ ዘንድ ማን ይችላል? በፊቱ ዕጣን ከማጠን በቀር ቤት እሠራለት ዘንድ እኔ ማን ነኝ? 7 አሁንም በወርቅና በብር፥ በናስና በብረት፥ በሐምራዊና በቀይ፥ በሰማያዊም ግምጃ መለበጥ የሚችልና፥ አባቴ ዳዊት ካዘጋጃቸው በእኔ ዘንድ በይሁዳና በኢየሩሳሌም ካሉት ብልሃተኞች ጋር ቅርጽ ማውጣት የሚያውቅ ብልሃተኛ ሰውን ላክልኝ። 8 ደግሞም አገልጋዮችህ ከሊባኖስ እንጨት መቍረጥ እንዲያውቁ እኔ አውቃለሁና ከሊባኖስ የዝግባና የጥድ፥ የሰንደልም እንጨት ላክልኝ። 9 የምሠራውም ቤት እጅግ ታላቅና ክቡር ይሆናልና ብዙ እንጨት ያዘጋጁልኝ ዘንድ፥ እነሆ፥ አገልጋዮች ከአገልጋዮችህ ጋር ይወጣሉ። 10 እነሆም፥ እንጨቱን ለሚቈርጡ ለአገልጋዮችህ ሃያ ሺህ የቆሮስ መስፈሪያ የተበጠረ ስንዴ፥ ሃያ ሺህም የቆሮስ መስፈሪያ ገብስ፥ ሃያ ሺህም የባዶስ መስፈሪያ የወይን ጠጅ፥ ሃያ ሺህም የባዶስ መስፈሪያ ዘይት በነጻ እሰጣለሁ።” 11 የጢሮስ ንጉሥ ኪራምም፥ “እግዚአብሔር ሕዝቡን ወድዶአልና በላያቸው አነገሠህ” ሲል ለሰሎሞን ጻፈለት። 12 የጢሮስ ንጉሥ ኪራምም ደግሞ አለ፥ “ለእግዚአብሔር ቤት ለመንግሥቱም ቤት ይሠራ ዘንድ ጥበበኛና ብልሃተኛ፥ አስተዋይም ልጅ ለንጉሡ ለዳዊት የሰጠ፥ ሰማይንና ምድርን የፈጠረ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ቡሩክ ይሁን። 13 አሁንም ብልሃተኛና አስተዋይ ሰው አቢኪራምን ልኬልሃለሁ። 14 እናቱ ከዳን ልጆች ናት፤ አባቱም የጢሮስ ሰው ነው፤ በወርቅና በብር፥ በናስና በብረት፥ ድንጋዩንና እንጨቱን መለበጥ፥ ሐምራዊውንና ሰማያዊውን፥ ቀዩንም ግምጃ፥ ጥሩውንም በፍታ መሥራት፥ ቅርጽም፥ ሌላም ነገር ሁሉ ማድረግ ያውቃል። ከብልሃተኞችህ ጋር ከጌታዬም ከአባትህ ከዳዊት ብልሃተኞች ጋር ሥራ ብለህ የምትሰጠውን ሁሉ አስቦ መሥራት ይችላል። 15 አሁንም ጌታዬ የተናገረውን ስንዴውንና ገብሱን ዘይቱንና የወይን ጠጁን ወደ አገልጋዮቹ ይላክ፤ 16 እኛም ከሊባኖስ የምትሻውን ያህል እንጨት እንቈርጣለን፤ በታንኳም አድርገን በባሕር ላይ ወደ አንተ ወደ ኢዮጴ እንልካለን፤ አንተም ወደ ኢየሩሳሌም ታስወስደዋለህ።” 17 ሰሎሞንም አባቱ ዳዊት ከቈጠራቸው ጋር ያልተቈጠሩ በእስራኤል ምድር የነበሩትን መጻተኞች ሁሉ ሰበሰበ፤ ቍጠራቸውም መቶ ኀምሳ ሦስት ሺህ ስድስት መቶ ሆኖ ተገኘ። 18 ከእነርሱም የሚሸከሙትን ሰባ ሺህ፥ በተራሮቹም ላይ የሚጠርቡትን ሰማንያ ሺህ፥ በሕዝቡም ሥራ ላይ የተሾሙትን ሦስት ሺህ ስድስት መቶ አደረገ። |