1 ነገሥት 20 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የናቡቴ በግፍ መገደል (በዕብ. ምዕ. 21 ነው።) 1 ለኢይዝራኤላዊው ለናቡቴ በሰማርያ ንጉሥ በአክዓብ ቤት አጠገብ የወይን ቦታ ነበረው። 2 አክዓብም ናቡቴን፥ “በቤቴ አቅራቢያ ነውና የአትክልት ቦታ አደርገው ዘንድ የወይን ቦታህን ስጠኝ፤ ስለ እርሱም ከእርሱ የተሻለ የወይን ቦታ እሰጥሃለሁ፤ ወይም ብትወድድ ዋጋውን ወርቅ እሰጥሃለሁ” ብሎ ተናገረው። 3 ናቡቴም አክዓብን፥ “የአባቶቼን ርስት እሰጥህ ዘንድ እግዚአብሔር አያምጣብኝ” አለው። 4 አክዓብም አዝኖ ሄደ፤ በአልጋውም ላይ ተኝቶ ፊቱን ተሸፋፈነ፤ እንጀራንም አልበላም። 5 ሚስቱም ኤልዛቤል ወደ እርሱ ገብታ፥ “ምን ያሳዝንሃል? እንጀራስ የማትበላ ምን ሆነሃል?” አለችው። 6 እርሱም፥ “ኢይዝራኤላዊውን ናቡቴን፦ የወይንህን ቦታ በገንዘብ ስጠኝ፤ ወይም ብትወድድ በፋንታው ሌላ የወይን ቦታ እሰጥሃለሁ ብዬ ተናገርሁት፤ እርሱ ግን የአባቶቼን ርስት አልሰጥህም ስለ አለኝ ነው” አላት። 7 ሚስቱ ኤልዛቤልም፥ “አሁንም አንተ የእስራኤል ንጉሥ ሆነህ እንደዚህ ታደርጋለህን? ተነሣ፤ እንጀራንም ብላ፤ ራስህንም አጽና፤ ልብህም ደስ ይበላት፤ የኢይዝራኤላዊውንም የናቡቴን የወይን ቦታ እሰጥሃለሁ” አለችው። 8 በአክዓብም ስም ደብዳቤ ጻፈች፤ በማኅተሙም አተመችው፤ በከተማው ወደ ነበሩትና ከናቡቴም ጋር ወደ ተቀመጡት ሽማግሌዎችና አለቆች ደብዳቤውን ላከች። 9 የዚያች ደብዳቤም ቃል እንዲህ ይላል፥ “ጾምን ጹሙ፤ ናቡቴንም በሕዝቡ መካከል በከፍተኛ ቦታ አስቀምጡት፤ 10 ሁለት የሐሰት ምስክሮችንም በፊቱ አስቀምጡና፦ እግዚአብሔርንና ንጉሡን ሰድቦአል ብለው ይመስክሩበት፤ አውጥታችሁም እስኪሞት ድረስ በድንጋይ መትታችሁ ግደሉት።” 11 በከተማውም የተቀመጡት የከተማው ሰዎችና ሽማግሌዎች፥ አለቆችም ኤልዛቤል እንዳዘዘቻቸውና ወደ እነርሱ በተላከው ደብዳቤ እንደ ተጻፈው እንዲሁ አደረጉ። 12 የጾም አዋጅም ነገሩ፤ ናቡቴንም በሕዝቡ ፊት በከፍተኛ ቦታ አስቀመጡት። 13 ሁለቱም የዐመፅ ልጆች የሆኑ ሰዎች ገብተው በፊቱ ቆሙ፤ “እግዚአብሔርንና ንጉሡን ሰድበሃል” ብለው መሰከሩበት። የዚያ ጊዜም ከከተማ አውጥተው በድንጋይ ደብድበው ገደሉት። 14 ወደ ኤልዛቤልም፥ “ናቡቴ በድንጋይ ተደብድቦ ሞተ” ብለው ላኩ። 15 ኤልዛቤልም በሰማች ጊዜ አክዓብን፥ “ናቡቴ ሞቶአል እንጂ በሕይወት አይደለምና በገንዘብ ይሰጥህ ዘንድ እንቢ ያለውን የኢይዝራኤላዊውን የናቡቴን የወይን ቦታ ተነሥተህ ውረስ” አለችው። 16 አክዓብም ኢይዝራኤላዊው ናቡቴ እንደ ሞተ በሰማ ጊዜ ወደ ኢይዝራኤላዊው ወደ ናቡቴ ወይን ቦታ ሊወርሰው ተነሥቶ ወረደ። 17 እግዚአብሔርም ቴስብያዊው ኤልያስን እንዲህ አለው፦ 18 “ተነሥተህ በሰማርያ የሚኖረውን የእስራኤልን ንጉሥ አክዓብን ትገናኝ ዘንድ ውረድ፤ እነሆ፥ ይወርሰው ዘንድ በወረደበት በናቡቴ የወይን ቦታ ውስጥ አለ። 19 እንዲህም ብለህ ንገረው፦ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ናቡቴን ገድለህ ወረስኸው፤ ስለዚህም ደግሞ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ጅቦችና ውሾች የናቡቴን ደም በላሱበት ስፍራ የአንተን ደም ደግሞ ውሾች ይልሱታል፤ አመንዝራዎችም በደምህ ይታጠባሉ” ብለህ ንገረው። 20 አክዓብም ኤልያስን፥ “ጠላቴ ሆይ! አገኘኸኝን?” አለው። እርሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት፥ “አግኝቼሃለሁ፤ ታስቈጣው ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ አድርገሃልና እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ 21 እነሆ፥ ክፉ ነገር አመጣብሃለሁ፤ እሳትን ከኋላህ አነድዳለሁ፤ ዐጥር ተጠግቶ እስከሚሸን ድረስ የአክዓብን ዘር አጠፋዋለሁ፤ በእስራኤል ውስጥ ያሉትንም፥ የሌሉትንም እነቅላለሁ፤ 22 በሥራህም አስቈጥተኸኛልና፥ እስራኤልንም አስተሃልና ቤትህን እንደ ናባጥ ልጅ እንደ ኢዮርብዓም ቤት እንደ አኪያም ልጅ እንደ ባኦስ ቤት አደርገዋለሁ።” 23 እግዚአብሔርም እንዲህ ብሎ ተናገረ፥ “በኢይዝራኤል ቅጥር አጠገብ ኤልዛቤልን ውሾች ይበሉአታል፥ 24 ከአክዓብም ወገን በከተማዪቱ ውስጥ የሞተውን ውሾች ይበሉታል፤ በሜዳውም የሞተውን የሰማይ ወፎች ይበሉታል።” 25 ነገር ግን አክዓብ በእግዚአብሔር ፊት ክፉን ያደርግ ዘንድ ራሱን ሸጠ፤ ሚስቱ ኤልዛቤል አስታዋለችና። 26 እግዚአብሔር ከእስራኤል ልጆች ፊት ያጠፋቸው አሞራውያን እንደ ሠሩት ሁሉ፥ ጣዖትን በመከተል እጅግ ርኩስ ነገርን ሠራ። 27 አክዓብም ይህን ቃል በሰማ ጊዜ ከእግዚአብሔር ፊት የተነሣ ደነገጠ፤ ልብሱንም ቀደደ፤ እያለቀሰም ሄደ፤ በሰውነቱም ላይ ማቅ ለበሰ፤ ጾመም፤ ኢይዝራኤላዊው ናቡቴንም በገደለበት ቀን ደግሞ ማቅ ለብሶ ነበር። 28 የእግዚአብሔርም ቃል ስለ አክዓብ ወደ ባሪያው ወደ ኤልያስ መጣ፤ እግዚአብሔርም አለው፦ 29 “አክዓብ በፊቴ እንደ ደነገጠ አየህን? በፊቴ በልጁ ዘመን በቤቱ ላይ ክፉ ነገር አመጣለሁ እንጂ በእርሱ ዘመን ክፉ ነገር አላመጣም።” |