እግዚአብሔር ይረዳቸዋል፤ ይታደጋቸዋልም፤ ከክፉዎች እጅ ነጥቆ ያወጣቸዋል፤ እርሱን መጠጊያ አድርገዋልና ያድናቸዋል።
በጦርነቱም ላይ ወደ እግዚአብሔር ጮኸው ስለ ነበር፣ በውጊያው ረዳቸው፤ አጋራውያንንና የጦር አጋሮቻቸውን ሁሉ አሳልፎ ሰጣቸው፤ ስለ ታመኑበትም ጸሎታቸውን ሰማ።
እግዚአብሔር ሆይ፤ ተነሥተህ ግጠማቸውና ጣላቸው፤ በሰይፍህም ከክፉዎች ታደገኝ።
ሥጋዬን ይበሉ ዘንድ፣ ክፉዎች ገፍተው በመጡ ጊዜ፣ ጠላቶቼና ባላጋራዎቼ በተነሡብኝ ጊዜ፣ እነርሱ ተሰነካክለው ወደቁ።
ዐጥንቶቹን ሁሉ ይጠብቃል፤ ከእነርሱም አንድ አይሰበርም።
“ለደረሰብኝ በደል ብድሬን ባልመልስ!” አትበል፤ እግዚአብሔርን ጠብቅ፤ እርሱ ይታደግሃል።
በዐናት ላይ እንደሚያንዣብቡ ወፎች፣ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ኢየሩሳሌምን እንዲሁ ይጋርዳታል፤ ይከልላታል፤ ይታደጋታል፤ በላይዋ ያልፋል፤ ያድናታልም።”
እስከ ሽምግልናችሁ፣ እስከ ሽበትም፣ የምሸከማችሁ እኔ ነኝ፤ እኔው ነኝ። ሠርቻችኋለሁ፤ እሸከማችኋለሁ፤ እደግፋችኋለሁ፤ አድናችኋለሁ።
ንጉሥ ሆይ፤ በሚንበለበለው የእቶን እሳት ውስጥ ብንጣል፣ የምናመልከው አምላክ ሊያድነን ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል።
ከዚያም ናቡከደነፆር እንዲህ አለ፤ “መልአኩን ልኮ አገልጋዮቹን ያዳነ፣ የሲድራቅ፣ የሚሳቅና የአብደናጎ አምላክ ይባረክ፤ በርሱ በመታመን የንጉሡን ትእዛዝ ጥሰው፣ ከአምላካቸው በቀር ሌላ አምላክ ለማገልገልም ሆነ ለርሱ ለመስገድ ፈቃደኛ ባለመሆን ሕይወታቸውን አሳልፈው ሰጥተዋልና።
ንጉሡ እጅግ ተደስቶ፤ ዳንኤልን ከጕድጓዱ እንዲያወጡት አዘዘ። ዳንኤል በአምላኩ ታምኖ ነበርና ከጕድጓድ በወጣ ጊዜ፣ አንዳች ጕዳት አልተገኘበትም።
ከእግዚአብሔር የተወለደ ሁሉ ኀጢአት እንደማያደርግ፣ ነገር ግን የእግዚአብሔር ልጅ እንደሚጠብቀው፣ ክፉውም እንደማይነካው እናውቃለን።