ኢሳይያስ 47 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የባቢሎን ውድቀት 1 አንቺ ድንግል የባቢሎን ልጅ ሆይ፥ ውረጂ፤ በትቢያም ላይ ተቀመጪ፤ የከለዳውያን ሴት ልጅ ሆይ፥ ከዚህ በኋላ ለስላሳና ቅምጥል አትባዪምና ያለ ዙፋን በመሬት ላይ ተቀመጪ። 2 ወፍጮ ወስደሽ ዱቄትን ፍጪ፤ ክንብንብሽን ግለጪ፤ ሽበትሽ ይታይ፤ ባትሽን ግለጪ፤ ወንዙንም ተሻገሪ። 3 ኀፍረትሽ ይገለጣል፤ ውርደትሽም ይታያል፤ ጽድቅ ከአንቺ ይወሰዳል፤ እንዲሁም በአንቺ ፋንታ ሰውን አሳልፌ አልሰጥም። 4 ታዳጊሽ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፥ ስሙ የእስራኤል ቅዱስ ነው። 5 የከለዳውያን ሴት ልጅ ሆይ፥ ከዚህ በኋላ፥ “የመንግሥታት እመቤት” አትባዪምና በድንጋጤ ዝም ብለሽ ተቀመጪ፤ ወደ ጨለማም ውስጥ ግቢ። 6 በሕዝቤ ላይ ተቈጥቼ ነበር፤ ርስቴንም አረከስሽ፤ በእጅሽም አሳልፌ ሰጠኋቸው፤ ለሽማግሌዎቻቸው አልራራሽም፤ ቀንበራቸውንም እጅግ አክብደሻል። 7 አንቺም፥ “እኔ ለዘለዓለም እመቤት እሆናለሁ” ብለሻል፤ ይህንም በልብሽ አላሰብሽም፤ ፍጻሜውንም አላስታወስሽም። 8 አሁንም አንቺ ቅምጥል ተዘልለሽ የምትቀመጪ፥ በልብሽም፥ “እኔ ነኝ ከእኔም በቀር ሌላ የለም፤ መበለትም ሆኜ አልኖርም፤ የወላድ መካንነትንም አላውቅም” የምትዪ፥ ይህን ስሚ፤ 9 አሁን ግን በአንድ ቀን እነዚህ ሁለት ነገሮች በድንገት ይመጡብሻል፤ የወላድ መካንነትና መበለትነት ስለ መተቶችሽ ብዛትና ስለ አስማቶችሽ ጽናት ፈጽመው ይመጡብሻል። 10 በክፋትሽ ታምነሻል፤ አንቺ ግን፥ “እኔ ነኝ፤ ከእኔ በቀር ሌላ የለም” ብለሻል፤ በዝሙትሽ ኀፍረት ያሰብሽውንም ዕወቂ፤ በልብሽ፥ “እኔ ነኝ ከእኔም በቀር ሌላ የለም” ብለሻልና። 11 ስለዚህ ምክንያት ጥፋት ይመጣብሻል፤ ጥልቀቱን አታውቂም፤ በውስጡም ትወድቂያለሽ፤ ጕስቁልና ይመጣብሻል፤ ማምለጥም አይቻልሽም፤ ሞት ድንገት ይመጣብሻል፤ አታውቂምም። 12 ምናልባትም ሊያድንሽ የሚችል እንደ አለ፥ ከአስማቶችሽና ከሕፃንነትሽ ጀምረሽ ከተማርሽው ከመተቶችሽ ብዛት ጋር ቁሚ። 13 በክፉ ምክርሽ ደክመሻል፤ አሁንም የሰማይን ከዋክብት የሚቈጥሩ፥ ከዋክብትንም የሚመለከቱ ይነሡ፤ ያድኑሽም፤ ምን እንደሚመጣብሽም ይንገሩሽ፤ 14 እነሆ፥ ሁሉም እንደ እብቅ እሳት ይቃጠላሉ፤ ሰውነታቸውንም ከነበልባል ኀይል አያድኑም፤ እንደ እሳትም ፍም ይሆኑብሻል፤ በላያቸውም ትቀመጫለሽ። 15 እነርሱ ረዳቶችሽ ይሆናሉ፤ ከሕፃንነትሽ ጀምረሽ ደከምሽ፤ ሰው በራሱ ይሳሳታል፤ ለአንቺ ግን መድኀኒት የለሽም። |