ዘፀአት 18 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ዮቶር ሙሴን እንደ መከረው 1 የምድያም ካህን የሙሴ አማት ዮቶር እግዚአብሔር ለሙሴና ለሕዝቡ ለእስራኤል ያደረገውን ሁሉ፥ እግዚአብሔርም እስራኤልን ከግብፅ እንደ አወጣ ሰማ። 2 በዚያ ጊዜ የሙሴ አማት ዮቶር ትቶአት የነበረውን የሙሴን ሚስት ሲፓራን፥ ሁለቱንም ልጆችዋን ወሰደ። 3 የአንደኛው ስም ጌርሳም ነበረ፤ አባቱ “በሌላ ሀገር ስደተኛ ነበርሁ” ብሎአልና፤ 4 የሁለተኛውም ስም አልዓዛር ነበረ፤ “የአባቴ አምላክ ረዳኝ፤ ከፈርዖንም እጅ አዳነኝ” ብሎአልና። 5 የሙሴ አማት ዮቶርም ከልጆቹና ከሚስቱ ጋር በእግዚአብሔር ተራራ አጠገብ በምድረ በዳ ወደ ሰፈረ ወደ ሙሴ መጣ። 6 ሙሴንም፥ “እነሆ፥ አማትህ ዮቶር፥ ሚስትህም ከእርስዋም ጋር ሁለቱ ልጆችህ መጥተውልሃል” አሉት። 7 ሙሴም አማቱን ሊገናኝ ወጣ፤ እጅ ነሣው፤ ሳመውም፤ እርስ በርሳቸውም ሰላምታ ተሰጣጡ፤ ወደ ድንኳኑም ገቡ። 8 ሙሴም እግዚአብሔር በፈርዖንና በግብፃውያን ላይ ስለ እስራኤል ያደረገውን ሁሉ፥ በመንገድም ያገኛቸውን ድካም ሁሉ፥ እግዚአብሔርም እንደ አዳናቸው ለአማቱ ነገረው። 9 ዮቶርም እግዚአብሔር ያደረገላቸውን ቸርነት ሁሉ፥ ከግብፃውያን እጅና ከፈርዖን እጅ እንደ አዳናቸው ሰምቶ በሁሉ አደነቀ። 10 ዮቶርም፥ “ከግብፃውያን እጅና ከፈርዖን እጅ ሕዝቡን የአዳነ እግዚአብሔር ቡሩክ ነው። 11 እግዚአብሔርም ግብፃውያን ከሚመኩባቸውና ከሚገዙላቸው አማልክት ሁሉ እንዲበልጥ አሁን ዐወቅሁ” አለ። 12 የሙሴ አማት ዮቶርም የሚቃጠል መሥዋዕትንና ሌላ መሥዋዕትን ለእግዚአብሔር ወሰደ፤ በእግዚአብሔርም ፊት ከሙሴ አማት ጋር እንጀራ ሊበሉ አሮንና የእስራኤል ሽማግሌዎች ሁሉ መጡ። የዳኞች መሾም ( ዘዳ. 1፥9-18 ) 13 እንዲህም ሆነ፤ በነጋው ሙሴ በሕዝቡ ሊፈርድ ተቀመጠ፤ ሕዝቡም በሙሴ ፊት ከጥዋት እስከ ማታ ድረስ ቆመው ነበር። 14 ዮቶርም ሙሴ በሕዝቡ ላይ የሚያደርገውን ሁሉ አይቶ እንዲህ አለው፥ “ብቻህን ተቀምጠህ በሕዝቡ የምታደርገው ይህ ምንድን ነው? ሕዝቡ ሁሉ ከጥዋት ጀምሮ እስከ ማታ ድረስ በዙሪያህ ቆመዋል።” 15 ሙሴም አማቱን፥ “ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ፍርድ ለመጠየቅ ወደ እኔ ይመጣሉ፤ 16 ነገርም ቢኖራቸው ወደ እኔ ይመጣሉ፤ በዚህና በዚያ ሰውም መካከል እፈርዳለሁ፤ የእግዚአብሔርንም ሥርዐትና ሕግ አስታውቃቸዋለሁ” አለው። 17 የሙሴም አማት አለው፥ “አንተ የምታደርገው ይህ ነገር ትክክል አይደለም። 18 አንተ፥ ከአንተም ጋር ያለው ሕዝብ ትደክማላችሁ፤ ይህ ነገር ይከብድብሃል፤ አንተ ብቻህን ልታደርገው አትችልም። 19 አሁንም እመክርሃለሁና ስማኝ፤ እግዚአብሔርም ከአንተ ጋር ይሆናል፤ አንተ በእግዚአብሔር ፊት ለሕዝቡ ሁን፤ ነገራቸውንም ወደ እግዚአብሔር አድርስ፤ 20 የእግዚአብሔርንም ሥርዐቱንና ሕጉን መስክርላቸው፤ የሚሄዱበትንም መንገድ፥ የሚያደርጉትንም ሥራ ሁሉ አሳያቸው። 21 አንተም ከሕዝቡ ሁሉ ኀያላን ሰዎችን፥ እግዚአብሔርን የሚፈሩትን እውነተኞች ሰዎችን፥ ትዕቢትንም የሚጠሉ ሰዎችን ፈልግ። ከእነርሱም የሺህ አለቆችን፥ የመቶ አለቆችን፥ የአምሳ አለቆችን፥ የዐሥርም አለቆችን ሹምላቸው። 22 በሕዝቡ ላይ ሁል ጊዜ ይፍረዱ፤ የከበዳቸውን ነገር ወደ አንተ ያምጡት፤ ቀላሉን ነገር ሁሉ እነርሱ ይፍረዱ፤ ያቃልሉልሃል፤ ይረዱሃልም። 23 ይህንም ቃሌን ብታደርግ፥ እግዚአብሔር ያበረታሃል፤ መፍረድም ትችላለህ፤ ሕዝቡም ሁሉ በሰላም ወደ ስፍራው ይመለሳል።” 24 ሙሴም የአማቱን ቃል ሰማ፤ እንደ አለውም አደረገ። 25 ሙሴም ከእስራኤል ሁሉ ችሎታ ያላቸውን ሰዎች መረጠ፤ በሕዝቡም ላይ የሺህ አለቆች፥ የመቶ አለቆች፥ የአምሳም አለቆች፥ የዐሥርም አለቆች አድርጎ ሾማቸው። 26 በሕዝቡም ላይ ሁልጊዜ ፈረዱ፤ የከበዳቸውንም ነገር ወደ ሙሴ አመጡ፤ ቀላሉን ነገር ሁሉ ግን እነርሱ ፈረዱ። 27 ሙሴም አማቱን አሰናበተው፤ እርሱም ወደ ሀገሩ ተመለሰ። |