መክብብ 6 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)1 ከፀሐይ በታች ያየሁት ክፉ ነገር አለ፥ እርሱም በሰው ላይ እጅግ የበዛ ነው። 2 እግዚአብሔር ለሰው ሀብትንና ጥሪትን ክብርንም ሰጠው፥ ከወደደውም ሁሉ ለሰውነቱ የከለከላት የለም፤ ነገር ግን ሌላ ሰው ይበላዋል እንጂ ከእርሱ ይበላ ዘንድ እግዚአብሔር አላሠለጠነውም፤ ይህም ከንቱና ክፉ ደዌ ነው። 3 ሰው መቶ ልጆች ቢወልድ፥ ብዙ ዘመንም በሕይወት ቢኖር፥ ዕድሜውም ብዙ ዓመት ቢሆን፥ ነገር ግን ነፍሱ መልካምን ባትጠግብ፥ መቃብርንም ባያገኝ፥ እኔ ስለ እርሱ፥ “ከእርሱ ይልቅ ጭንጋፍ ይሻላል” አልሁ። 4 በከንቱ መጥቶአል፥ በጨለማም ይሄዳል፥ ስሙ በጨለማ ይሸፈናልና። 5 ደግሞም ፀሐይን አላየም፥ አላወቀምም፤ ስለዚህ ከዚያ ይልቅ ለዚህ ዕረፍት አለው። 6 ሺህ ዓመት ሁለት ጊዜ በሕይወት ቢኖር፥ መልካምንም ባያይ፥ ሁሉ ወደ አንድ ስፍራ የሚሄድ አይደለምን? 7 የሰው ድካም ሁሉ በአፉ ነው፥ ነፍሱ ግን አትጠግብም። 8 ከአላዋቂ ይልቅ ለጠቢብ ጥቅሙ ምንድር ነው? በሕያዋን ፊትስ መሄድን ለሚያውቅ ለድሃ ጥቅሙ ምንድር ነው? 9 በዐይን ማየት በነፍስ ከመቅበዝበዝ ይሻላል፥ ይህ ደግሞ ከንቱ ነው፥ ነፋስንም እንደ መከተል ነው። 10 የሆነው ሁሉ እነሆ፥ ስሙ አስቀድሞ ተጠራ፥ ሰውም እንደ ሆነ ታወቀ፤ ከእርሱም ከሚበረታው ጋር ይፋረድ ዘንድ አይችልም። 11 ከንቱን የሚያበዛ ብዙ ነገር አለና፥ ለሰው ጥቅሙ ምንድር ነው? 12 ሰው በከንቱ ወራቱ ቍጥርና እንደ ጥላ በሚያሳልፈው ዘመኑ በሕይወቱ ሳለ ለሰው የሚሻለውን የሚያውቅ ማን ነው? ወይስ ለሰው ከፀሓይ በታች ከእርሱ በኋላ የሚሆነውን ማን ይነግረዋል? |