አሞጽ 8 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ፍሬ የሞላበት ዕንቅብ 1 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ አሳየኝ፤ እነሆም የቃርሚያ ፍሬ የሞላበት ዕንቅብ ነበረ። 2 እርሱም፥ “አሞጽ ሆይ! የምታየው ምንድን ነው?” አለኝ። እኔም፥ “የቃርሚያ ፍሬ የሞላበት ዕንቅብ ነው” አልሁት። እግዚአብሔርም አለኝ፥ “ፍጻሜ በሕዝቤ በእስራኤል ላይ መጥቶአል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ደግሞ ይቅር አልላቸውም። 3 ያንጊዜም በመቅደሶቻቸው ዋይ ዋይ ይላሉ” ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ በየስፍራው የሚወድቀው ሬሳ ይበዛልና፤ እነርሱም ይጠፋሉና። የእስራኤል ውድቀት 4 ችግረኛውን በጥዋት የምታስጨንቁ፥ የሀገሩንም ድሃ የምትቀሙ እናንተ ሆይ! 5 “እህልን እንሸጥ ዘንድ መባቻው መቼ ያልፋል? የኢፍ መስፈሪያውንም እያሳነስን፥ ሰቅሉንም እያበዛን፥ በሐሰተኛም ሚዛን እያታለልን፥ 6 ድሃውን በብር፥ ችግረኛውንም በአንድ ጥንድ ጫማ እንገዛ ዘንድ፥ በእህላችንም ንግድ እንድንጠቀም ሰንበት መቼ ያልፋል? የምትሉ እናንተ ሆይ! ይህን ስሙ።” 7 እግዚአብሔር በያዕቆብ ትዕቢት እንዲህ ብሎ ምሎአል፥ “ሥራችሁን ሁሉ ለዘለዓለም ምንም አልረሳም። 8 በውኑ ምድሪቱ ስለዚህ ነገር አትናወጥምን? በእርስዋም የሚኖር ሁሉ አያለቅስምን? ጦርነት እንደ ወንዝ ይፈስሳል፤ እንደ ግብፅም ወንዝ ይሞላል፤ ደግሞም ይወርዳል። 9 በዚያም ቀን ፀሐይ በቀትር ይገባል፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ብርሃንም በምድር ላይ በቀን ይጨልማል። 10 ዓመት በዓላችሁንም ወደ ልቅሶ፥ ዝማሬያችሁንም ወደ ዋይታ እለውጣለሁ፤ ማቅንም በወገብ ሁሉ ላይ፥ ቡሃነትንም በራስ ሁሉ ላይ ላይ አመጣለሁ፤ እንደ ወዳጅ ልቅሶ አደርጋችኋለሁ፤ ከእርሱም ጋር ያሉት እንደ መከራ ቀን ይሆናሉ። 11 “እነሆ በምድር ላይ ራብን የምሰድድበት ዘመን ይመጣል፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ እርሱም የእግዚአብሔርን ቃል ከመስማት እንጂ እንጀራን ከመራብና ውኃን ከመጠማት አይደለም። 12 ከባሕርም እስከ ባሕር ድረስ፥ ከሰሜንም እስከ ምሥራቅ ድረስ ይቅበዘበዛሉ፤ የእግዚአብሔርንም ቃል ለመሻት ይርዋርዋጣሉ፤ አያገኙትምም። 13 በዚያ ቀን መልከ መልካሞቹ ደናግልና ጐበዛዝቱ በጥም ይዝላሉ። 14 ዳን ሆይ፥ ሕያው አምላክህን! ደግሞም፦ ሕያው የቤርሳቤህን አምላክ ብለው በሰማርያ መማፀኛ የሚምሉ፥ እነርሱ ይወድቃሉ፥ ደግሞም አይነሡም።” |