መዝሙር 129 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉምከእስራኤል ጠላቶች ለመዳን የቀረበ መዝሙር 1 ከወጣትነቴ ጀምሮ አደጋ ደርሶብኛል፤ እስራኤላውያን እንዲህ ይበሉ፦ 2 “ከወጣትነቴ ጀምሮ ጠላቶቼ በጭካኔ አሳደዱኝ፤ ነገር ግን አላሸነፉኝም። 3 ጀርባዬን በጅራፍ ተልትለው፥ የታረሰ ማሳ አስመስለውታል። 4 እግዚአብሔር ሁልጊዜ ትክክለኛ ነው፤ ከእነዚያ ጨካኞች ገመድ ነጻ አውጥቶኛል።” 5 ጽዮንን የሚጠላ ሁሉ ይሸነፍ! ወደ ኋላውም ይመለስ! 6 በቤት ጣራ ላይ እንደሚበቅልና ከማደጉ በፊት እንደሚደርቅ ሣር ይሁን። 7 እንዲህ ዐይነቱን ሣር ማንም አይሰበስበውም፤ ወይም ነዶው በእጁ አይሞላም። 8 በአጠገባቸው የሚያልፉት ሁሉ ለጽዮን ጠላቶች “እግዚአብሔር ይባርካችሁ! እኛም በእግዚአብሔር ስም እንባርካችኋለን!” አይሉአቸውም። |