መዝሙር 139 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ለመዘምራን አለቃ የዳዊት መዝሙር። 1 “አቤቱ፥ ከክፉ ሰው አድነኝ፥ ከዐመፀኛ ሰውም ታደገኝ፥ 2 ሁልጊዜ በልባቸው ዐመፃን የሚመክሩ፥ ይገድሉኝ ዘንድ ይከብቡኛል። 3 ምላሳቸውን እንደ እባብ ሳሉ፤ ከከንፈራቸው በታች የእባብ መርዝ አለ። 4 አቤቱ፥ ከኃጥኣን እጅ ጠብቀኝ፥ እርምጃዬንም ሊያሰናክሉ ከመከሩ ከዐመፀኞች ሰዎች አድነኝ። 5 ትዕቢተኞች ወጥመድን ሰወሩብኝ፥ ለእግሮቼም የወጥመድ ገመድን ዘረጉ፤ በመንገዴም ዕንቅፋትን አኖሩ። 6 እግዚአብሔርንም፥ “አንተ አምላኬ ነህ፤ የልመናዬን ቃል፥ አቤቱ፥ አድምጥ” አልሁት። 7 አቤቱ፥ ጌታዬ፥ የድኅነቴ ኀይል፥ በጦርነት ቀን በራሴ ላይ ሁነህ ሰወርኸኝ። 8 አቤቱ፥ ጌታዬ፥ ከምኞቴ የተነሣ ለኀጢአተኞች አትስጠኝ፤ በላዬ ተማከሩ፥ እንዳይታበዩም አትተወኝ። 9 የአሽክላቸው ራስ የከንፈራቸውም ክፋት ይድፈናቸው። 10 የእሳት ፍም በላያቸው ይውደቅ፤ መቆም እንዳይችሉ በችግር ወደ ምድር ይውደቁ። 11 ተናጋሪ ሰው በምድር ውስጥ አይጸናም፤ ዐመፀኛ ሰውን ክፋት ለጥፋት ታድነዋለች። 12 እግዚአብሔር ለድሆች ዳኝነትን ለችግረኞችም ፍርድን እንዲያደርግ ዐወቅሁ። 13 ጻድቃን ግን በእውነት ስምህን ያመሰግናሉ፤ ቅኖችም በፊትህ ይኖራሉ። |