መሳፍንት 17 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ሚካ ያስቀረፃቸው ጣዖቶች 1 በተራራማውም በኤፍሬም ሀገር ሚካ የተባለ አንድ ሰው ነበረ። 2 እናቱንም፥ “ከአንቺ ዘንድ የተሰረቀው፥ የረገምሽበትም፥ በጆሮዬም የተናገርሽበት አንድ ሺህ አንድ መቶ ብር እነሆ፥ በእኔ ዘንድ አለ፤ እኔም ወስጄው ነበር” አላት። እናቱም፥ “ልጄ ሆይ፥ እግዚአብሔር ይባርክህ” አለችው። 3 አንዱን ሺህ አንድ መቶ ብርም ለእናቱ መለሰላት፤ እናቱም፥ “ይህን ብር የተቀረፀ ምስልና ቀልጦ የተሠራ ምስል አድርጌ ከእጄ ስለ ልጄ ለእግዚአብሔር እቀድሰዋለሁ፤ አሁንም ለአንተ እመልሰዋለሁ” አለች። 4 ለእናቱም ገንዘቡን መለሰላት እናቱም ብሩን ወስዳ ከእርሱ ሁለቱን መቶ ብር ለአንጥረኛ ሰጠችው፤ እርሱም የተቀረፀ ምስልና ቀልጦ የተሠራ ምስል አደረገው። በሚካም ቤት አስቀመጡት። 5 ሰውዬውም ሚካ የአማልክት ቤት ነበረው፤ ኤፉድና ተራፊም አደረገ፤ ከልጆቹም አንዱን ቀደሰው፤ ካህንም ሆነለት። 6 በዚያም ዘመን በእስራኤል ዘንድ ንጉሥ አልነበረም፤ ሰውም ሁሉ በፊቱ መልካም መስሎ የታየውን ያደርግ ነበር። 7 በይሁዳ ቤተ ልሔምም ከይሁዳ ወገን የሆነ አንድ ጐልማሳ ነበረ፤ እርሱም ሌዋዊ ነበረ፤ በዚያም ይቀመጥ ነበር። 8 ይህም ሰው በአገኘው ስፍራ ይኖር ዘንድ ከይሁዳ ከተማ ከቤተ ልሔም ሄደ፤ በዚያም ያድር ዘንድ ወደ ተራራማው ወደ ኤፍሬም ሀገር ወደ ሚካ ቤት ደረሰ። 9 ሚካም፥ “ከወዴት መጣህ?” አለው። እርሱም፥ “ከይሁዳ ቤተ ልሔም የሆንሁ ሌዋዊ ነኝ፤ የምቀመጥበትንም ስፍራ ለመሻት እሄዳለሁ” አለው። 10 ሚካም፥ “በእኔ ዘንድ ተቀመጥ፤ አባትና ካህንም ሁነኝ፤ እኔም ልብሶችንና ምግብህን፥ በየዓመቱም ዐሥር ብር እሰጥሃለሁ” አለው። 11 ሌዋዊዉም ሄደ። ከዚያም ሰው ጋር ይኖር ዘንድ ጀመረ፤ ጐልማሳውም ከልጆቹ እንደ አንዱ ሆነለት። 12 ሚካም ሌዋዊዉን እጁን ቀባው፤ ጐልማሳውም ካህን ሆነለት፤ በሚካም ቤት ኖረ። 13 ሚካም፥ “ሌዋዊ ካህን ስለ ሆነልኝ እግዚአብሔር መልካም እንዲሠራልኝ አሁን አውቃለሁ” አለ። |