ኢዮብ 39 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)1 “ዋልያ የምትወልድበትን ጊዜ ታውቃለህን? የምታምጥበትንስ ጊዜ ትመለከታለህን? 2 እርስዋ የምትወልድበትንስ ሙሉ ወራት ትቈጥራለህን? ከምጥስ ትገላግላታለህን? 3 ልጆቻቸውንስ ያለ ፍርሃት አሳድገሃልን? መከራቸውንስ አስወግደሃልን? 4 ልጆቻቸው ያመልጣሉ። ይባዛሉ፥ ይዋለዳሉም። ይወጣሉ፥ ወደ እነርሱም አይመለሱም። 5 “የሜዳውንስ አህያ ነጻነት ማን አወጣው? ከእስራቱስ ማን ፈታው? 6 በረሃውን ለእርሱ ቤት፥ መኖሪያውንም በጨው ምድር አድርጌ ሰጠሁት። 7 በከተማው ሕዝብ ውካታ ይዘብታል፤ የሚያስፈራውንም ጩኸት አይሰማም። 8 ተራራውን እንደ መሰምሪያው ይመለከተዋል፥ ለምለሙንም ሁሉ ይፈልጋል። 9 “ጎሽ ያገለግልህ ዘንድ ይፈቅዳልን? ወይስ በግርግምህ አጠገብ ያድራልን? 10 በቀንበር ትጠምደዋለህን? በእርሻህስ ውስጥ ትልም ያርስልሃልን? 11 ጕልበቱስ ብርቱ ስለሆነ ትታመነዋለህን? ተግባርህንስ ለእርሱ ትተዋለህን? 12 ዘርህንስ ይመልስልህ ዘንድ፥ በአውድማህስ ያከማችልህ ዘንድ ትታመነዋለህን? 13 “ሰጎን ክንፍዋን በደስታ ታንቀሳቅሳለች፥ በፀነሰችም ጊዜ ልትበላ ትመኛለች፥ 14 ዕንቍላልን በመሬት ላይ ትጥላለች፥ በአፈርም ውስጥ ታሞቀዋለች፥ 15 እግር ይሰብረው ዘንድ፥ የምድረ በዳም አውሬ ይረግጠው ዘንድ ትረሳለች። 16 የእርስዋ እንዳልሆኑ በልጆችዋ ላይ ትጨክናለች፤ ያለ ፍርሀትም በከንቱ ትሠራለች፤ 17 እግዚአብሔር ጥበብን ከእርስዋ ከልክሎአልና፥ ማስተዋልንም አልሰጣትምና። 18 በዘመንዋ ወደ ላይ ራስዋን ከፍ ከፍ ታደርጋለች፥ በፈረሱና በፈረሰኛው ትሣለቃለች። 19 “ለፈረስ አንተ ጕልበቱን ሰጥተኸዋልን? አንገቱንስ ጋማ አልብሰኸዋልን? 20 በፍጹም የጦር መሣሪያ አስጊጠኸዋልን? እምቢያውንስ በብርታት የከበረ አድርገኸዋልን? 21 በኮቴው በሸለቆው ውስጥ ይጐደፍራል፥ በጕልበቱም ወደ ሜዳ ይወጣል። 22 በሚገናኘው ፍላጻ ላይ ይስቃል። ከሰይፍም ፊት አይመለስም። 23 ቀስትና ጦር በእርሱ ላይ ይበረታሉ፥ 24 በቍጣውም መሬትን ያጠፋል፤ የመለከትም ድምፅ እስከሚሰማው አያምንም። 25 የመለከትም ድምፅ ሲሰማ፦ እሰይ ይላል፤ ከሩቅም ሆኖ ሰልፍንና የአለቆችን ጩኸት፥ የሠራዊቱንም ውካታ ያሸታል። 26 “በውኑ ከጥበብህ የተነሣ ጭልፊት ያንዣብባልን? ወይስ ክንፎቹን ወደ ደቡብ ይዘረጋልን? 27 በአፍህ ትእዛዝ ንስር ከፍ ከፍ ይላልን? ጆፌ አሞራስ ልጆቹን አቅፎ ያድራልን? 28 በዓለቱ ገደል ላይ ይኖራል፤ በገደሉ ገመገምና በጥጉ ያድራል። 29 በዚያም ሆኖ የሚበላውን ይፈልጋል፤ ዐይኖቹም በሩቁ ይመለከታሉ። 30 ጫጭቶቹም ወደ ደም ይሮጣሉ፥ በድን ወደ አለበትም ስፍራ ወዲያውኑ ይደርሳሉ።” |