ኢዮብ 21 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የኢዮብ መልስ 1 ኢዮብም መለሰ፤ እንዲህም አለ፦ 2 “እኛ አጽናናነው እንዳትሉኝ፥ ስሙ፤ ቃሌን ስሙ። 3 እናገር ዘንድ ዝም በሉ፤ ከተናገርሁ በኋላ ትስቁብኛላችሁና፤ 4 ሰው የሚዘልፈኝ አይደለም፤ ስለ ምንስ አልቈጣም? 5 ወደ እኔ ተመልከቱ፥ ተደነቁም፤ እጃችሁንም በጕንጫችሁ ላይ አኑሩ። 6 እኔ ባሰብሁ ቍጥር እጨነቃለሁ፤ ጻዕርም ሥጋዬን ይይዛል። 7 ስለ ምን ኀጢኣተኞች በሕይወት ይኖራሉ? በባለጠግነትስ ስለ ምን ያረጃሉ? 8 ዘራቸው በፊታቸው ከእነርሱ ጋር ጸንቶ ይኖራል፤ ልጆቻቸውም በዐይናቸው ፊት ናቸው። 9 ቤታቸው በብልፅግና የተሞላ ነው፤ የሚያስፈራቸውም የለም። ከእግዚአብሔርም ዘንድ መቅሠፍት አይመጣባቸውም። 10 በሬዎቻቸው አይመክኑም፤ ላሞቻቸውም አይጨነግፉም፤ በደኅናም ይወልዳሉ። 11 እነርሱም እንደ በጎች ለዘለዓለም ይጠበቃሉ፤ ልጆቻቸውም በፊታቸው ይዘፍናሉ። 12 በገናና መሰንቆ ይዘው ይዘምራሉ፤ በመዝሙራቸውም ደስ ይላቸዋል። 13 ዕድሜያቸውንም በተድላ ይፈጽማሉ፤ በሲኦል ማረፊያም ይጋደማሉ። 14 እግዚአብሔርንም፦ እንዲህ ይሉታል፦ ከእኛ ዘንድ ራቅ፤ መንገድህንም እናውቅ ዘንድ አንወድድም። 15 እንገዛለትስ ዘንድ እርሱ ምን ይችላል? ወይስ ወደ እርሱ ብንቀርብ ምን ይጠቅመናል? 16 “እነሆ፥ በጎነታቸው በእጃቸው ውስጥ አለች፤ የኃጥኣንን ሥራ አይመለከትም። 17 የኃጥኣን መብራት ትጠፋለች፤ መቅሠፍትም ትመጣባቸዋለች። የበቀል ቍጣም ይይዛቸዋል፤ 18 በነፋስም ፊት እንደ ገለባ፥ አውሎ ነፋስም እንደሚወስደው ትቢያ ይሆናሉ። 19 ልጆቹ ሀብቱን አያገኙም። እግዚአብሔር ብድራቱን ይከፍለዋል። እርሱም ያንጊዜ ያውቃል። 20 ዐይኖቹ ልጆቹ ሲወጉ ያያሉ፤ እግዚአብሔርም አያድናቸውም። 21 የወደደውን በቤቱ ውስጥ ያደርጋል። ወራቶቹም ከቍጥር ድንገት ይጐድላሉ። 22 ጥንቱን ዕውቀትንና ምክርን የሚያስተምር እግዚአብሔር አይደለምን? በነፍሰ ገዳዩስ የሚፈርድ እርሱ አይደለምን? 23 አንድ ሰው በሰላም ተዘልሎ ሲቀመጥ፥ በሁሉም ፈጽሞ ደስ ብሎት ሳለ ይሞታል። 24 በውስጡ ስብ ሞልቶአል፥ የአጥንቶቹም ቅልጥም ፈስሶአል። 25 ሌላውም ሰው መልካምን ነገር ከቶ ሳይበላ በተመረረች ነፍሱ ይሞታል። 26 ሁሉም በአፈር ውስጥ በአንድ ላይ ይተኛሉ፤ ትሎችም ይሸፍኗቸዋል። 27 እነሆ፥ ደፍራችሁ፥ በእኔ ላይ በጠላትነት እንደ ተነሣችሁ ዐውቄአለሁ። 28 እናንተ፦ የአለቃው ቤት የት ነው? ኀጢአተኛውም ያደረበት ድንኳን የት ነው? ብላችኋልና። 29 መንገድ ዐላፊዎችን ጠይቋቸው፤ ምልክታቸውንም አታገኙም። 30 ኀጢአተኛውን ክፉ ቀን ትጠብቀዋለች፤ በቍጣ ቀንም ይወስዱታል። 31 መንገዱን በፊቱ የሚናገር ማን ነው? እርሱ የሠራውንስ የሚመልስበት ማን ነው? 32 እርሱን ግን ወደ መቃብር ይወስዱታል፤ በመቃብሩም ውስጥ ይጠበቃል። 33 የሸለቆው ጓል ይጣፍጥለታል፤ በኋላውም ሰው ሁሉ ይወጣል፤ በፊቱም ቍጥር የሌለው ሰው አለ። 34 ለምን በከንቱ ታጽናኑኛላችሁ? በእናንተ ዘንድ ግን ዕረፍት የለኝም።” |