ኢዮብ 15 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የኤልፋዝ ሁለተኛ ንግግር 1 ቴማናዊውም ኤልፋዝ መለሰ፥ እንዲህም አለ፦ 2 “በውኑ ጠቢብ ሰው እንደ ነፋስ በሆነ ዕውቀት ይመልሳልን? ሆዱንስ በሥቃይ ይሞላልን? 3 ከከንቱ ነገር፥ ወይስ ከማይጠቅም ንግግር ጋር ይዋቀሳልን? 4 አንተ እግዚአብሔርን መፍራት ትተሃልን? በእግዚአብሔርስ ፊት እንዲህ ያለውን ቃል ትናገራለህን? 5 ከአፍህ ንግግር የተነሣ መጠንህ ይታወቃል፥ የኀያላኑንም ቃል አልለየህም። 6 የሚፈርድብህ አፍህ ነው እንጂ እኔ አይደለሁም፤ ከንፈሮችህም ይመሰክሩብሃል። 7 በውኑ ከሰው ቀድመህ የተፈጠርህ ሰው አንተ ነህን? ወይስ ከተራሮች በፊት ተፀነስህን? 8 የእግዚአብሔርንስ ትእዛዝ ሰምተሃልን? ወይስ እግዚአብሔር አማካሪው አድርጎሃልን? ወይስ ጥበብን ለብቻህ አድርገሃልን? 9 እኛ የማናውቀውን አንተ ምን ታውቃለህ? እኛስ የማናስተውለውን አንተ ምን ታስተውላለህ? 10 በዕድሜ ከአባትህ የሚበልጡ፥ ሽበትም ያላቸው ሽማግሎች ከእኛ ጋር አሉ። 11 ጥቂት ብትበድል ተገረፍህ፥ ይህም የተናገርኸው ነገር በዐቅምህ አይደለም። 12 “ልብህስ ለምን ይደፍራል? ዐይኖችህስ ለምን ይገላምጣሉ? 13 በእግዚአብሔር ፊት በቍጣ ትመልስ ዘንድ፤ እንደዚህስ ያለ ነገር ከአፍህ ታወጣ ዘንድ፤ 14 ንጹሕ ይሆን ዘንድ ሟች ሰው ማን ነው? ጻድቅስ ይሆን ዘንድ ከሴት የተወለደ ማን ነው? 15 እነሆ፥ በቅዱሳኑ እንኳ አይታመንም፤ ሰማይም በፊቱ ንጹሕ አይደለም። 16 ይልቁንስ አስጸያፊና የረከሰ፥ ኀጢአትንም እንደ ውኃ የሚጠጣ ሰው ምንኛ ያንስ? 17 “ስማኝ ልንገርህ፥ እነሆም ያየሁትን እነግርሃለሁ፤ 18 ጠቢባን የተናገሩትን፥ አባቶቻቸውም ያልሰወሩትን እነግርሃለሁ። 19 ምድር ለእነርሱ ብቻ ተሰጥታለችና፤ በመካከላቸውም እንግዳ ሕዝብ አልገባባቸውምና። 20 የኃጥእ ሰው ዕድሜው በጭንቅ ያልፋል፥ ለግፈኛ የተመደቡ ዓመታቱም ሁሉ የተቈጠሩ ናቸው። 21 የሚያስደነግጥ ድምፅም በጆሮው ነው፤ በደኅንነትም ይኖር ዘንድ ተስፋ በሚያደርግበት ጊዜ ጥፋት ይመጣበታል። 22 ከጨለማ ተመልሶ እንዲወጣ ተስፋ የለውም፥ ለሰይፍም ኀይል ፈጽሞ ተዳርጎአል። 23 ለአሞራዎችም ምግብ ሆኖ ተሰጥቶአል በድን ሆኖ እንደሚቈይም እርሱ ራሱ ያውቃል። የጨለማ ቀንም እንደ አውሎ ነፋስ ትወስደዋለች። 24 መከራና ጭንቀት ይመጡበታል፤ በፊት እንደ ተሰለፈ መኰንን ይወድቃል። 25 እጁን በእግዚአብሔር ላይ ዘርግቶአልና፥ ሁሉን በሚችል አምላክ ፊትም አንገቱን አደንድኖአልና። 26 በደንዳና አንገቱና በወፍራሙ በጋሻው ጕብጕብ፥ ከውርደት ጋር እየሰገገ ይመጣበታልና። 27 በስብም ፊቱን ከድኖአልና ስቡንም በወገቡ ላይ አድርጎአልና፥ 28 በተፈቱም ከተሞች ውስጥ ይኖራል፥ ሰውም በሌለባቸው ቤቶች ይገባል፥ እርሱ ያዘጋጀውንም ሌሎች ይወስዱታል። 29 “እርሱ ባለጠጋ አይሆንም፤ ሀብቱም አይጸናም፤ ጥላውንም በምድር ላይ አይጥልም፤ 30 ከጨለማ በምንም አያመልጥም፤ ነፋስም ቅርንጫፎቹን ያደርቃቸዋል፥ አበባዎቹም ይረግፋሉ። 31 ለመኖር ተስፋ አያደርግም፤ ፍጻሜው ከንቱ ይሆናልና። 32 ቀኑ ሳይደርስ መከሩ ይጠፋል፥ ቅርንጫፉም አይለመልምም። 33 ጮርቃውም ይረግፋል፤ እንደ ወይራም አበባ ይወድቃል። 34 ለኃጥኣን ሁሉ ሞት ምስክራቸው ነው፥ እሳት የጉቦ ተቀባዮችን ቤት ይበላል። 35 በሆዳቸው ጭንቅትን ይፀንሳሉ፥ ከንቱ ነገርንም ይወልዳሉ። ሆዳቸውም ተንኰልን ያዘጋጃል።” |