ሕዝቅኤል 35 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)በኤዶምያስ ላይ የተነገረ ትንቢት 1 የእግዚአብሔርም ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦ 2 “የሰው ልጅ ሆይ! ፊትህን ወደ ሴይር ተራራ መልስ፤ ትንቢትም ተናገርበት፤ 3 እንዲህም በለው፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የሴይር ተራራ ሆይ! እነሆ በአንተ ላይ ነኝ፤ እጄን እዘረጋብሃለሁ፤ ባድማና ውድማም አደርግሃለሁ። 4 ከተሞችህንም አፈራርሳቸዋለሁ፤ አንተም ባድማ ትሆናለህ፤ እኔም እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃለህ። 5 የዘለዓለም ጠላት ሁነሃልና፥ በመከራቸውም ጊዜ በኀይለኛይቱ የኀጢአታቸው ቀጠሮ ጊዜ የእስራኤልን ልጆች በሰይፍ እጅ ጥለሃቸዋልና፤ 6 ስለዚህ እኔ ሕያው ነኝ! በደም እንደ በደልህ ደም ያሳድድሃል፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር። 7 የሴይርንም ተራራ ውድማ አደርገዋለሁ፤ ሰውንና እንስሳውንም አጠፋለሁ። 8 ተራሮችህንም በተገደሉት ሰዎች እሞላለሁ፤ በኮረብቶችህና በሸለቆዎችህ፥ በፈሳሾችህም ሁሉ ላይ በሰይፍ የተገደሉት ሁሉ ይወድቃሉ። 9 ለዘለዓለምም ባድማ አደርግሃለሁ፤ ከተሞችህም ሰው የማይኖርባቸው ይሆናሉ፤ እኔም እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃለህ። 10 “እግዚአብሔርም በዚያ ሳለ፥ አንተ፥ እነዚህ ሁለቱ ሕዝቦች፥ እነዚህም ሁለቱ ሀገሮች ለእኔ ይሆናሉ፤ እኔም እወርሳቸዋለሁ ብለሃልና፤ 11 ስለዚህ እኔ ሕያው ነኝ! እንደ ቍጣህ መጠን፥ እነርሱንም ጠልተህ እንዳደረግኸው እንደ ቅንአትህ መጠን እኔ እፈርድብሃለሁ፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ በፈረድሁብህም ጊዜ በእነርሱ ዘንድ የታወቅሁ እሆናለሁ። 12 አንተም፦ ፈርሰዋል፤ መብልም ሆነው ለእኛ ተሰጥተዋል ብለህ በእስራኤል ተራሮች ላይ የተናገርኸውን ስድብ ሁሉ እኔ እግዚአብሔር እንደ ሰማሁት ታውቃለህ። 13 አንተ አፍህን በእኔ ላይ ከፍ ከፍ እንደ አደረግህ እኔ ሰምቼአለሁ።” 14 ጌታ እግዚአብሔርም እንዲህ ይላል፥ “ምድር ሁሉ ደስ ሲላት አንተን ባድማ አደርግሃለሁ። 15 የእስራኤል ቤት ርስት ባድማ ስለ ሆነ በላዩ ደስ እንዳለህ፥ እንዲሁ አደርግብሃለሁ፤ የሴይር ተራራ ሆይ! አንተና መላው ኤዶምያስ ባድማ ትሆናላችሁ፤ እኔም እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃለህ።” |