ሕዝቅኤል 25 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)በአሞን ላይ የተነገረ ትንቢት 1 የእግዚአብሔርም ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦ 2 “የሰው ልጅ ሆይ! ፊትህን ወደ አሞን ልጆች አቅንተህ ትንቢት ተናገርባቸው። 3 ለአሞንም ልጆች እንዲህ በል፦ የጌታን የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ መቅደሴ በረከሰ ጊዜ የእስራኤልም ምድር ባድማ በሆነች ጊዜ፥ የይሁዳም ቤት በተማረኩ ጊዜ ስለ እነርሱ ደስ ብሎሃልና፤ 4 ስለዚህ እነሆ ርስት አድርጌ ለምሥራቅ ልጆች አሳልፌ እሰጥሃለሁ፤ እነርሱም ማደሪያዎቻቸውን በአንተ ዘንድ ይሠራሉ፤ ድንኳኖቻቸውንም በአንተ ውስጥ ይተክላሉ፤ ፍሬህን ይበላሉ፤ ወተትህንም ይጠጣሉ። 5 የአሞንን ከተማ ለግመሎች ማሰማሪያ፥ የአሞንንም ልጆች ለመንጋ መመሰጊያ አደርጋለሁ፤ እኔም እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ። 6 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና፦ በእጆችህ አጨብጭበሃልና፥ በእግሮችህም አሸብሽበሃልና፥ ሰውነትህም በእስራኤል ምድር ላይ ደስ ብሎአታልና፤ 7 ስለዚህ እነሆ እጄን ዘርግቼብሃለሁ፤ ለአሕዛብም አስበዘብዝሃለሁ፤ ከአሕዛብም ለይች እቈርጥሃለሁ፤ ከሀገሮችም እደመስስሃለሁ፤ አጠፋሃለሁም፤ እኔም እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃለህ።” በሞአብ ላይ የተነገረ ትንቢት 8 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ “ሞአብና ሴይር፦ እነሆ የይሁዳ ቤት እንደ አሕዛብ ሁሉ ነው ብለዋልና፤ 9 ስለዚህ እነሆ የሞአብን ጫንቃ ከከተሞቹ፥ በዳርቻው ካሉት የምድሩ ትምክሕት ከሆኑት ከተሞቹ፥ ከቤትየሺሞት፥ ከባኣልሜዎን፥ ከቂርያታይም አደክማለሁ። 10 የአሞን ልጆች በአሕዛብ መካከል ከእንግዲህ ወዲህ እንዳይታሰቡ የአሞንን ልጆች ለምሥራቅ ልጆች ርስት አድርጌ እሰጣቸዋለሁ። 11 በሞአብም ላይ በቀልን አደርጋለሁ፤ እኔም እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ።” በኤዶም ላይ የተነገረ ትንቢት 12 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ኤዶምያስ በይሁዳ ቤት ላይ በቀል አድርጎአልና፥ ቂምም ይዞአልና፥ በቀልንም ተበቅሎአልና፤ 13 ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እጄን በኤዶምያስ ላይ እዘረጋለሁ፤ ከእርስዋም ዘንድ ሰውንና እንስሳን አጠፋለሁ፤ ባድማም አደርጋታለሁ፤ ከቴማንና ከድዳንም ያመለጡ በሰይፍ ይወድቃሉ። 14 በሕዝቤ በእስራኤል እጅ ኤዶምያስን እበቀላለሁ፤ እንደ ቍጣዬና እንደ መዓቴም መጠን በኤዶምያስ ያደርጋሉ፤ በቀሌንም ያውቃሉ፥” ይላል ጌታ እግዚአብሔር። በፍልስጥኤም ላይ የተነገረ ትንቢት 15 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ “ፍልስጥኤማውያን በቀልን አድርገዋልና፥ በቀላቸውንም አጽንተዋልና፥ እስራኤልም ለዘለዓለም ይጠፉ ዘንድ ነፍሳቸው ደስ ይላታልና፤ 16 ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እነሆ እጄን በፍልስጥኤማውያን ላይ እዘረጋለሁ፤ መኳንንቱንም እቈርጣለሁ፤ የባሕሩንም ዳር ቅሬታ አጠፋለሁ። 17 በመዓት መቅሠፍትም ታላቅ በቀል አደርግባቸዋለሁ፤ በቀሌንም በላያቸው በአደረግሁ ጊዜ፥ እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ።” |