ሕዝቅኤል 23 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ሁለት አመንዝራ እኅትማማቾች 1 የእግዚአብሔር ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦ 2 “የሰው ልጅ ሆይ፥ የአንዲት እናት ልጆች የሆኑ ሁለት ሴቶች ነበሩ። 3 በግብፅ ሀገር አመነዘሩ፤ በኮረዳነታቸው ሳሉ አመነዘሩ፤ በዚያም ጡቶቻቸው ወደቁ፤ በዚያም ድንግልናቸውን አጡ። 4 ስማቸውም የታላቂቱ ሐላ የታናሽ እኅቷም ሐሊባ ነበረ፤ እኔም አገባኋቸው፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆችንም ወለዱ። ስማቸውም ሐላ ሰማርያ ናት፤ ሐሊባ ደግሞ ኢየሩሳሌም ናት። 5 “ሐላም አመነዘረችብኝ፤ ወዳጆችዋንም የሚቀርቡአትን አሦራውያንን በፍቅር ተከተለቻቸው። 6 እነርሱም ሰማያዊ ሐር የለበሱ መሳፍንትና መኳንንት፥ መልከ መልካሞች ጐበዛዝት፥ በፈረስ ላይ የሚቀመጡ የተመረጡ ፈረሰኞች ነበሩ። 7 ዝሙቷንም ከተመረጡ ከአሦር ሰዎች ሁሉ ጋር አደረገች፤ በፍቅር በተከተለቻቸውም ጣዖቶቻቸው ሁሉ ረከሰች። 8 በግብፅም የነበረውን ዝሙቷን አልተወችም፤ በዚያም በኮረዳነቷ ጊዜ ከእርስዋ ጋር ተኝተው ነበር፤ የድንግልናዋንም ጡቶች ዳብሰው ነበር፤ ዝንየታቸውንም አፍስሰውባት ነበር። 9 ስለዚህ በፍቅር በተከተለቻቸው በወዳጆችዋ በአሦራውያን እጆች አሳልፌ ሰጠኋት። 10 እነርሱም ኀፍረተ ሥጋዋን ገለጡ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆችዋንም ማርከው ወሰዱ፤ እርስዋንም በሰይፍ ገደሉ፤ በእርስዋና በሴቶች ልጆችዋ ላይ በቀልን ስላደረጉባቸው በሴቶች መካከል መተረቻ ሆነች። 11 “እኅቷም ሐሊባ ይህን አየች፤ ሆኖም ከእርስዋ ይልቅ በፍቅር በመከተልዋ ረከሰች፤ ዝሙቷንም ከእኅቷ ዝሙት ይልቅ አበዛች። 12 የሚቀርቡአትን መሳፍንቱንና መኳንንቱን ጌጠኛ ልብስ የለበሱትን፥ በፈረሶች ላይ የሚቀመጡትን ፈረሰኞች፥ ሁሉንም መልከ መልካሞችን ጐበዛዝት አሦራውያንን በፍቅር ተከተለቻቸው። 13 እንደ ረከሱም አየሁ፤ ሁለቱም አንድ መንገድ ሄደዋል። 14 ዳግመኛም ዝሙቷን አበዛች፤ በግንብ ላይ የተሣሉ የከለዳውያን ሰዎች ሥዕልንም አየሁ። 15 በጥቍር ቀለም የተሣሉ የከለዳውያንን መልክ አየሁ፤ በወገባቸው ዝናር የታጠቁ ናቸው፤ በራሳቸውም ላይ ጥልፍ ሰበን የጠመጠሙ ናቸው፤ ፊታቸውም ሦስት ወገን ነው፤ ሁሉም በትውልድ ሀገራቸው የሚኖሩ የባቢሎን ሰዎችን ከለዳውያንን ይመስላሉ። 16 ዐይንዋንም ወደ እነርሱ አቅንታ አየቻቸው፤ ወደ ከላውዴዎንም ምድር ወደ እነርሱ መልእክተኞችን ላከች። 17 የባቢሎንም ልጆች ወደ እርስዋ መጥተው በመኝታዋ ከእርስዋ ጋር ተኙ፤ በዝሙታቸውም አረከሱአት፤ እርስዋም ከእነርሱ ጋር ረከሰች፤ ነፍስዋም ከእነርሱ ተለየች። 18 ዝሙቷንም ገለጠች፤ ኀፍረተ ሥጋዋንም ገለጠች፤ ነፍሴም ከእኅቷ እንደ ተለየች እንዲሁ ነፍሴ ከእርስዋ ተለየች። 19 ነገር ግን በግብፅ ምድር ያመነዘረሽበትን የወጣትነትሽን ዘመን አስበሽ ዝሙትሽን አበዛሽ። 20 አካላቸውም እንደ አህዮች አካል፤ ዘራቸውም እንደ ፈረሶች ዘር የሆነውን እነዚያን የከለዳውያን ልጆች በፍቅር ተከተልሻቸው። 21 ጡትሽ በአጐጠጐጠ ጊዜ በማደሪያሽ በግብፅ ሀገር የሠራሽውን የወጣትነትሽን ኀጢአት አሰብሽ።” 22 ስለዚህ ሐሊባ ሆይ! ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ “ነፍስሽ ከእነርሱ የተለየች ወዳጆችሽን አስነሣብሻለሁ፤ በዙሪያሽም በአንቺ ላይ አመጣቸዋለሁ። 23 እነርሱም የባቢሎን ልጆች፥ ከለዳውያንም ሁሉ፥ ፋቁድ፥ ሱሔ፥ ቆዓ፥ ከእነርሱም ጋር አሦራውያን ሁሉ፥ መልከ መልካሞች ጐበዛዝት፥ መሳፍንትና መኳንንት ሁሉ፥ መሳፍንትና አማካሪዎች ሁሉ፥ በሦስት ወገን በፈረስ ላይ የተቀመጡ ናቸው። 24 ስማቸውን ያስጠሩ ሰዎች ሁሉ በመንኰራኵርና በሠረገላ፥ በአሕዛብም ጉባኤ ይመጡብሻል፤ ጋሻና አላባሽ ጋሻ፥ ራስ ቍርም ይዘው በዙሪያሽ ጥበቃ ያደርጋሉ፤ ፍርድንም እሰጣቸዋለሁ፤ እንደ ፍርዳቸውም ይፈርዱብሻል። 25 ቅንአቴንም በአንቺ ላይ አደርጋለሁ፤ በመዓትም ያደርጉብሻል፤ አፍንጫሽንና ጆሮሽንም ከአንቺ ይቈርጣሉ፤ ከአንቺም የቀረ በሰይፍ ይወድቃል፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆችሽንም ማርከው ይወስዳሉ፤ ከአንቺም የቀሩትን እሳት ትበላቸዋለች። 26 ልብስሽንም ይገፍፉሻል፤ የክብርሽንም ጌጥ ይወስዳሉ። 27 ሴሰኝነትሽንም፥ ከግብፅ ምድር ያወጣሽውን ዝሙትሽንም ከአንቺ አስቀራለሁ፤ ዐይንሽንም ከእንግዲህ ወዲህ ወደ እነርሱ አታነሺም፤ ግብፅንም ከዚያ ወዲያ አታስቢም። 28 ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እነሆ በጠላሻቸው እጅ፥ ነፍስሽም በተለየቻቸው እጅ አሳልፌ እሰጥሻለሁ፤ 29 እነርሱም በጥል ያደርጉብሻል፤ የደከምሽበትንም ሁሉ ይወስዳሉ፤ ዕራቁትሽንና ዕርቃንሽን አድርገውም ይተዉሻል፤ የግልሙትናሽንም ነውር፥ ሴሰኝነትሽንና ግልሙትናሽንም ሁሉ ይገልጣሉ። 30 ከአሕዝብ ጋር ስላመነዘርሽ፤ በበደላቸውም ስለ ረከስሽ ይህን ያደርጉብሻል። 31 በእኅትሽ መንገድ ሄደሻል፤ ስለዚህ ጽዋዋን በእጅሽ እሰጥሻለሁ። 32 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የጠለቀውንና የሰፋውን፥ ብዙም የሚይዘውን የእኅትሽን ጽዋ ትጠጪአለሽ፤ ብዙ መጠጥን በሚጠጡ ሰዎችም ዘንድ መሳቂያና መሳለቂያ ትሆኛለሽ። 33 በእኅትሽ በሰማርያ ጽዋ፥ በድንጋጤና በጥፋት ጽዋ፥ በስካርና በውርደት ትሞሊያለሽ። 34 ትጠጪዋለሽ፥ ትጨልጪውማለሽ፤ በዓላትሽንና መባቻዎችሽን እሽራለሁ፤ እኔ ተናግሬአለሁና ይላል እግዚአብሔር። 35 ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ዘንግተሽኛልና፥ ወደ ኋላሽም ጥለሽኛልና አንቺ ደግሞ ሴሰኝነትሽንና ኀጢአትሽን ተሸከሚ።” 36 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፥ “የሰው ልጅ ሆይ! ሐላንና ሐሊባን ተፋረዳቸው፤ ኀጢአታቸውንም አስታውቃቸው፤ 37 አመንዝረዋልና፥ ደምም በእጃቸው አለና፥ ዝሙታቸውንም ወድደዋልና፥ ለእኔም የወለዱአቸውን ልጆቻቸውን መብል እንዲሆኑላቸው በእሳት አሳልፈዋቸዋልና። 38 ይህን ደግሞ አድርገውብኛል፤ በዚያ ቀን መቅደሴን አርክሰዋል፤ ሰንበታቴንም ሽረዋል። 39 ልጆቻቸውንም ለጣዖቶቻቸው በሠዉ ጊዜ ፥ በዚያው ቀን ያረክሱት ዘንድ ወደ መቅደሴ ገቡ፤ እነሆም በቤቴ ውስጥ እንደዚህ አደረጉ። 40 ከሩቅ ሀገርም ወደመጡ ሰዎች መልእክተኞችን ላኩ፤ እነርሱም በደረሱ ጊዜ ይታጠባሉ፤ ዐይኖቻቸውንም ይኳላሉ፤ ያጌጣሉም። 41 በክብር አልጋ ላይ ይቀመጣሉ፤ በፊት ለፊታቸውም ማዕድ ተዘጋጅታ ነበር፤ በዕጣኔና በዘይቴም ደስ ይላቸዋል። 42 የበገናውን አውታር ድምፅ ይቃኛሉ፤ ከብዙ ሰዎችም ጉባኤ ጋር ሰካራሞቹ ከምድረ በዳ መጡ፤ በእጃቸው አንባር፥ በራሳቸውም የተዋበ አክሊል አደረጉ። 43 እኔም፦ ‘አሁን ከእርስዋ ጋር ያመነዝራሉ፤ እርስዋም ከእነርሱ ጋር ታመነዝራለች፤’ አልሁ። 44 ወደ ጋለሞታ እንደሚገቡም ወደ እርስዋ ገቡ፤ እንዲሁ ይሰስኑ ዘንድ ወደ ሐላና ወደ ሐሊባ ገቡ። 45 ሴቶቹ አመንዝሮች ናቸውና፥ በእጃቸውም ደም አለና ጻድቃን ሰዎች በአመንዝሮቹና በደም አፍሳሾቹ ሴቶች ላይ በሚፈረደው ፍርድ ይፈርዱባቸዋል።” 46 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፥ “ጉባኤን አመጣባቸዋለሁ፤ ለመበተንና ለመበዝበዝም አሳልፌ እሰጣቸዋለሁ። 47 ጉባኤውም በድንጋይ ይወግሩአቸዋል፤ በሰይፋቸውም ይቈርጡአቸዋል፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸውንም ይገድላሉ፤ ቤቶቻቸውንም በእሳት ያቃጥላሉ። 48 ሴቶችም ሁሉ እንደ ኀጢአታችሁ እንዳይሠሩ ይማሩ ዘንድ ሴሰኝነትን ከምድር ላይ አጠፋለሁ። 49 እንግዲህ በደላችሁ በላያችሁ ላይ ይመለሳል፤ እናንተም የጣዖቶቻችሁን ኀጢአት ትሸከማላችሁ፤ እኔም ጌታ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ።” |