ሕዝቅኤል 17 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ምዕራፍ 17። የንስርና የወይን ተክል ምሳሌ 1 የእግዚአብሔር ቃል ወደኔ እንዲህ ሲል መጣ፦ 2 “የሰው ልጅ ሆይ! ለእስራኤል ቤት ምሳሌ መስለህ ንገር፤ እንዲህም በል፦ 3 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ታላቅ ክንፍ፥ ረጅምም ጽፍር ያለው፥ ላባንም የተሞላ፥ መልከ ዝንጉርጉር የሆነ ታላቅ ንስር ወደ ሊባኖስ መጣ፤ የዝግባንም ጫፍ ወሰደ። 4 ቀንበጡንም ቀነጠበ፤ ወደ ከነዓንም ምድር ወሰደው፤ ቅጥር ባለው ከተማም አኖረው። 5 ከምድርም ዘር ወሰደ፤ በፍሬያማ እርሻም ዘራው፤ በብዙም ውኃ አጠገብ እንደ አኻያ ዛፍ አኖረው። 6 በበቀለም ጊዜ ቁመቱ ያጠረ፥ ሐረጉም ወደ እርሱ የሚመለስ፥ ሥሩም በበታቹ የነበረ ሰፊ ወይን ሆነ፤ እንዲሁ ወይን ሆነ፤ ሐረግም ሰደደ፤ ቀንበጥም አወጣ። 7 “ታላቅ ክንፍና ብዙ ጽፍርም ያለው ሌላ ታላቅ ንስር ነበረ፤ እነሆም ያጠጣው ዘንድ ይህ ወይን ሥሩን ወደ እርሱ ሰደደ፤ ሐረጉንም ከተተከለበት ከመደቡ ወደ እርሱ አዘነበለ። 8 ሐረግም ያወጣ፥ ፍሬም ያፈራ፥ የከበረ ወይንም ይሆን ዘንድ በመልካም መሬት ውስጥ፥ በብዙም ውኃ አጠገብ ተተክሎ ነበር። 9 እንዲህም በል፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ በውኑ ይከናወንለት ይሆን? ይደርቅስ ዘንድ፥ አዲስ የበቀለውስ ቅጠሉ ይጠወልግ ዘንድ ሥሩን አይነቅለውምን? ፍሬውንስ አይለቅመውምን? ሥሩም የተነቀለው በብርቱ ክንድና በብዙ ሕዝብ አይደለም። 10 ተተክሎስ፥ እነሆ ይከናወንለት ይሆን? የምሥራቅ ነፋስ ባገኘው ጊዜ ፈጽሞ አይደርቅምን? በተተከለበት መደብ ላይ ይደርቃል።” የምሳሌው ትርጓሜ 11 የእግዚአብሔርም ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦ 12 “የሰው ልጅ ሆይ፥ ለአስቈጡኝ ለእስራኤል ቤት ይህ ትርጓሜ ምን እንደ ሆነ አታውቁምን? በላቸው። እንዲህም ብለህ ንገራቸው፦ እነሆ የባቢሎን ንጉሥ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፤ ንጉሥዋንና መኳንንቶችዋንም ማረከ፤ ወደ ሀገሩም ወደ ባቢሎን ወሰዳቸው። 13 ከመንግሥትም ዘር ወስዶ ከእርሱ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ፤ አማለውም፤ የምድሪቱንም ኀያላን ወሰደ፤ 14 ይኸውም መንግሥቱ እንድቷረድና ከእንግዲህም ከፍ እንዳትል፥ ቃል ኪዳኑን በመጠበቅ ጸንታ እንድትኖር ነው። 15 እርሱ ግን በእርሱ ላይ ሸፈተ፤ ፈረሶችንና ብዙንም ሕዝብ ይሰጡት ዘንድ መልእክተኞችን ወደ ግብፅ ላከ። በውኑ ይከናወንለት ይሆን? ይህንስ ያደረገ ያመልጣልን? ቃል ኪዳንንስ ያፈረሰ ያመልጣልን? 16 “እኔ ሕያው ነኝ! ያነገሠውና መሐላውን የናቀበት፥ ቃል ኪዳኑንም ያፈረሰበት ንጉሥ በሚኖርበት ስፍራ ከእርሱ ጋር በባቢሎን መካከል በርግጥ ይሞታል፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር። 17 ብዙዎችን ነፍሳት ለማስወገድ ምሽግን በመሸጉ፥ ቅጥርንም በሠሩ ጊዜ፥ ፈርዖን በታላቅ ኀይልና በብዙ ሕዝብ በጦርነት አይረዳውም። 18 ቃል ኪዳኑንም በማፍረስ መሐላውን ንቆአል፤ እነሆም እጁን አሳልፌ ሰጠሁ፤ ይህንም ሁሉ አድርጎአል፤ ስለዚህም አያመልጥም። 19 ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እኔ ሕያው ነኝ! የናቀውን መሐላዬንና ያፈረሰውን ቃል ኪዳኔን በራሱ ላይ አመጣለሁ በላቸው። 20 መረቤንም በእርሱ ላይ እዘረጋለሁ፤ በወጥመድም ይያዛል፤ ወደ ባቢሎንም አመጣዋለሁ፤ በእኔም ላይ ስላደረገው ዐመፅ በዚያ ከእርሱ ጋር እፋረዳለሁ። 21 ያመለጡትም ሁሉ በሰይፍ ይወድቃሉ፤ የቀሩትም ሁሉ ወደ እየነፋሳቱ ይበተናሉ፤ እኔም እግዚአብሔር እንደ ተናገርሁ ታውቃላችሁ። ከእግዚአብሔር የተሰጠ ተስፋ 22 “ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ከረዥሙ ዝግባ ጫፍ ላይ ቀንበጥን ወስጄ አኖረዋለሁ፤ ከጫፎቹም አንዱን ቀንበጥ እቀነጥበዋለሁ፤ በረዥምና በታላቅ ተራራም ላይ እተክለዋለሁ። 23 ከፍ ባለው በእስራኤል ተራራ ላይ እተክለዋለሁ፤ ቅርንጫፎችንም ያወጣል፤ ፍሬም ያፈራል፤ ታላቅም ዝግባ ይሆናል፤ በበታቹም ወፎች ሁሉ ያርፋሉ፤ በቅርንጫፎቹም ጥላ በክንፍ የሚበርር ሁሉ ይጠጋል፤ ቅርንጫፉም ይሰፋል። 24 የዱር ዛፎች ሁሉ፥ ረዥሙን ዛፍ ዝቅ ያደረግሁ፥ አጭሩንም ዛፍ ከፍ ያደረግሁ፥ የለመለመውንም ዛፍ ያደረቅሁ፥ የደረቀውንም ዛፍ ያለመለምሁ እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ፤ እኔ እግዚአብሔር ተናገርሁ፤ እኔም አደረግሁ።” |