2 ዜና መዋዕል 19 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ነቢዩ ኢዩ የይሁዳን ንጉሥ ኢዮሣፍጥን እንደ ገሠጸው 1 የይሁዳም ንጉሥ ኢዮሣፍጥ ወደ ቤቱ ወደ ኢየሩሳሌም በሰላም ተመለሰ። 2 ነቢዩ የአናኒ ልጅ ኢዩ ሊገናኘው ወጣ፤ ንጉሡንም ኢዮሣፍጥን፥ “ኀጢአተኛውን ታግዛለህን? ወይስ እግዚአብሔር የሚጠላውን ትወድዳለህን? ስለዚህም ነገር ከእግዚአብሔር ዘንድ ቍጣ መጥቶብሃል። 3 ነገር ግን የማምለኪያ ዐፀዶችን ከምድረ ይሁዳ አስወግደሃልና፥ እግዚአብሔርንም ትፈልግ ዘንድ ልብህን አዘጋጅተሃልና መልካም ነገር ተገኝቶብሃል” አለው። 4 ኢዮሣፍጥም በኢየሩሳሌም ተቀመጠ፤ ደግሞም ከቤርሳቤህ ጀምሮ እስከ ተራራማው እስከ ኤፍሬም ሀገር ድረስ ወደ ሕዝቡ ወጥቶ ወደ አባቶቻቸው አምላክ ወደ እግዚአብሔር መለሳቸው። 5 በተመሸጉት በይሁዳ ከተሞች ሁሉ በእያንዳንዱ ከተማ ውስጥ ፈራጆችን ሾመ። 6 ፈራጆቹንም፥ “ለእግዚአብሔር እንጂ ለሰው አትፈርዱምና፥ የፍርድም ነገር ከእናንተ ጋር ነውና የምታደርጉትን ተመልከቱ። 7 አሁንም እግዚአብሔርን መፍራት በእናንተ ላይ ይሁን፤ በአምላካችንም በእግዚአብሔር ዘንድ በደልና ለሰው ፊት ማድላት፥ መማለጃም መውሰድ የለምና ሁሉን ተጠንቅቃችሁ አድርጉ” አላቸው። 8 ኢዮሣፍጥም ከሌዋውያንና ከካህናት፥ ከእስራኤልም የአባቶች ቤቶች አለቆች በእግዚአብሔር ፍርድ በኢየሩሳሌም በሚኖሩ ላይ ፍርድን እንዲፈርዱ በኢየሩሳሌም ሾመ። 9 እንዲህም ብሎ አዘዛቸው፥ “እንዲሁ እግዚአብሔርን በመፍራት፥ በቅንነትም፥ በፍጹምም ልብ አድርጉ።” 10 በከተሞቻቸውም ከተቀመጡት ከወንድሞቻችሁ በደምና በደም መካከል፥ በሕግና በትእዛዝ፥ በሥርዐትና በፍርድም መካከል ያለ ማናቸውም ሰው ለፍርድ ወደ እናንተ ቢመጣ እግዚአብሔርን እንዳይበድሉ፥ ቍጣም በእናንተና በወንድሞቻችሁ ላይ እንዳይመጣ አስጠንቅቁአቸው፤ እንዲህም ብታደርጉ በደለኞች አትሆኑም። 11 እነሆም፥ ለእግዚአብሔር በሚሆነው ነገር ሁሉ የካህናቱ አለቃ አማርያ፥ በንጉሡም ነገር ሁሉ የይሁዳ ቤት አለቃ የይስማኤል ልጅ ዝባድያስ በላያችሁ ተሾመዋል፤ ጸሐፍቱና ሌዋውያኑ ደግሞ በፊታችሁ አሉ፤ በርትታችሁም አድርጉ፤ እግዚአብሔር መልካም ከሚያደርግ ጋር ይሁን። |