መዝሙር 109 - አዲሱ መደበኛ ትርጒምመዝሙር 109 ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር። 1 የምስጋናዬ ምንጭ የሆንህ አምላክ ሆይ፤ ዝም አትበል፤ 2 ክፉዎችና አታላዮች፣ አፋቸውን ከፍተውብኛልና፤ በውሸተኛ አንደበት ተናግረውብኛል። 3 በጥላቻ ቃል ከብበውኛል፤ ያለ ምክንያትም ጥቃት አድርሰውብኛል። 4 ስወድዳቸው ይወነጅሉኛል፤ እኔ ግን እጸልያለሁ። 5 በበጎ ፈንታ ክፋትን፣ በወደድኋቸው ፈንታ ጥላቻን ይመልሱልኛል። 6 ክፉ ሰው በላዩ ሹም፤ ከሳሽም በቀኙ ይቁም። 7 ፍርድ ፊት ሲቆም በደለኛ ሆኖ ይገኝ፤ ጸሎቱም ለፍርድ ትሁንበት። 8 ዕድሜው ይጠር፤ ሹመቱንም ሌላ ይውሰደው። 9 ልጆቹ ድኻ አደጎች ይሁኑ፤ ሚስቱም መበለት ትሁን። 10 ልጆቹ ይንከራተቱ፤ ለማኞችም ይሁኑ፤ ከፈረሰው ቤታቸውም ይሰደዱ። 11 ያለውን ሁሉ ዕዳ ጠያቂ ይውረሰው፤ የድካሙንም ዋጋ ባዕዳን ይቀሙት። 12 ማንም ሰው ምሕረት አያድርግለት፤ ለድኻ አደግ ልጆቹም የሚራራ አይኑር። 13 ዘሩ ተለይቶ ይጥፋ፤ ስማቸውም በሚቀጥለው ትውልድ ይደምሰስ። 14 የአባቶቹ በደል በእግዚአብሔር ፊት ይታሰብ፤ የእናቱም ኀጢአት አይደምሰስ። 15 መታሰቢያቸውን ከምድር ያጠፉ ዘንድ፣ ኀጢአታቸው ሁልጊዜ በእግዚአብሔር ፊት ይኑር። 16 ድኻውንና ችግረኛውን፣ ልቡም የቈሰለውን፣ እስከ ሞት አሳደደ እንጂ፣ ምሕረት ያደርግ ዘንድ አላሰበምና። 17 መራገምን ወደደ፤ ወደ እርሱም መጣች፤ በመባረክ ደስ አልተሠኘም፤ በረከትም ከርሱ ራቀች። 18 መርገምን እንደ ልብስ ለበሳት፤ እርሷም እንደ ውሃ ወደ ውስጥ ሰውነቱ፣ እንደ ዘይትም ወደ ዐጥንቱ ዘለቀች። 19 ገላውን እንደሚሸፍንበት ልብስ፣ ዘወትር እንደሚታጠቀውም መቀነት ትሁነው። 20 እግዚአብሔር ለሚወነጅሉኝ ሰዎች፣ በነፍሴም ላይ ክፉ ለሚናገሩ የሚከፍላቸው ይኸው ይሁን። 21 አንተ ግን ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ ስለ ስምህ በበጎ ተመልከተኝ፤ ምሕረትህም መልካም ናትና አድነኝ። 22 እኔ ድኻና ችግረኛ ነኝና፤ ልቤም በውስጤ ቈስሏልና። 23 እንደ ምሽት ጥላ ከእይታ ተሰውሬአለሁ፤ እንደ አንበጣም ረግፌአለሁ። 24 ከጾም የተነሣ ጕልበቴ ዛለ፤ ሰውነቴም ከስቶ ዐመድ ለበሰ። 25 ለመሣለቂያ ሆንሁላቸው፤ ሲያዩኝም ራሳቸውን ይነቀንቃሉ። 26 እግዚአብሔር አምላኬ ሆይ፤ ርዳኝ፤ እንደ ምሕረትህም አድነኝ። 27 እግዚአብሔር ሆይ፤ እጅህ ይህን እንዳደረገች፣ አንተም ይህን እንደ ፈጸምህ ይወቁ። 28 እነርሱ ይራገማሉ፤ አንተ ግን ትባርካለህ፤ በሚነሡበት ጊዜ ይዋረዳሉ፤ ባሪያህ ግን ሐሤት ያደርጋል። 29 የሚወነጅሉኝ ውርደትን ይከናነቡ፤ ዕፍረትንም እንደ ሸማ ይልበሱ። 30 እግዚአብሔርን በአንደበቴ እጅግ አመሰግናለሁ፤ በታላቅ ሕዝብም መካከል አወድሰዋለሁ። 31 በነፍሱ ላይ ከሚፈርዱት ያድነው ዘንድ፣ እርሱ በችግረኛው ቀኝ በኩል ይቆማልና። |
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.
Biblica, Inc.