ሰቈቃወ 3 - አዲሱ መደበኛ ትርጒምא አሌፍ א አሌፍ 1 በቍጣው በትር፣ መከራ ያየ ሰው እኔ ነኝ። 2 ከፊቱ አስወጣኝ፤ በብርሃን ሳይሆን በጨለማ እንድሄድ አደረገኝ። 3 በርግጥ ቀኑን ሁሉ በመደጋገም፣ እጁን በላዬ ላይ መለሰ። ב ቤት ב ቤት 4 እርሱ ሥጋዬንና ቈዳዬን አስረጀ፤ ዐጥንቶቼንም ሰባበረ። 5 በምሬትና በድካም፣ ቅጥር ሠራብኝ፤ ዙሪያዬንም ከበበኝ። 6 ከሞቱ ብዙ ጊዜ እንደ ሆናቸው፣ በጨለማ እንድኖር አደረገኝ። ג ጊሜል ג ጊሜል 7 በቅጥር ውስጥ ዘጋብኝ፤ ስለዚህ ማምለጥ አልቻልሁም፤ የእስር ሰንሰለቴንም አከበደብኝ። 8 ርዳታ ፈልጌ ብጣራና ብጮኽ እንኳ፣ ጸሎቴን መስማት አልፈለገም። 9 መንገዴን በተጠረቡ ድንጋዮች ዘጋ፤ ጐዳናዬንም አጣመመ። ד ዳሌት ד ዳሌት 10 አሸምቆ እንደ ተኛ ድብ፣ እንደ አደባም አንበሳ፣ 11 ከመንገድ ጐትቶ አስወጣኝ፤ ቈራረጠኝም፤ ያለ ረዳትም ተወኝ። 12 ቀስቱን ገተረ፤ ለፍላጻዎቹም ዒላማ አደረገኝ። ה ሄ ה ሄ 13 ፍላጻዎችን ከሰገባው አውጥቶ፣ ልቤን ወጋው። 14 ለሕዝቤ ሁሉ ማላገጫ ሆንሁኝ፤ ቀኑን ሙሉ በመሣለቅ ያዜሙብኛል። 15 መራራ ሥር አበላኝ፤ ሐሞትም አጠገበኝ። ו ዋው ו ዋው 16 ጥርሴን በድንጋይ ሰበረ፤ በትቢያ ውስጥ ረጋገጠኝ። 17 ነፍሴ ሰላምን ዐጣች፤ ደስታ ምን እንደ ሆነ ረሳሁ። 18 ስለዚህ፣ “ክብሬ፣ ከእግዚአብሔርም ተስፋ ያደረግሁት ሁሉ ሄዷል” አልሁ። ז ዛይን ז ዛይን 19 የጭንቀቴንና የመንከራተቴን፣ ምሬትንና ሐሞትን ዐስባለሁ። 20 ዘወትር አስበዋለሁ፤ ነፍሴም በውስጤ ተዋርዳለች። 21 ሆኖም ይህን ዐስባለሁ፤ እንግዲያስ ተስፋ አለኝ፤ ח ኼት ח ኼት 22 ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ታላቅ ፍቅር የተነሣ ነው፤ ርኅራኄው አያልቅምና። 23 ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው፤ ታማኝነትህም ብዙ ነው። 24 ራሴን እንዲህ አልሁት፤ “እግዚአብሔር ዕድል ፈንታዬ ነው፤ ስለዚህ ተስፋ አደርገዋለሁ።” ט ቴት ט ቴት 25 እርሱን ተስፋ ለሚያደርጉት፣ ለሚፈልገውም ሰው እግዚአብሔር መልካም ነው። 26 ሰው የእግዚአብሔርን ማዳን፣ ዝም ብሎ ተስፋ ቢያደርግ መልካም ነው። 27 ሰው በወጣትነቱ፣ ቀንበር ቢሸከም መልካም ነው። י ዮድ י ዮድ 28 ብቻውን ዝም ብሎ ይቀመጥ፤ እግዚአብሔር አሸክሞታልና። 29 ፊቱን በዐቧራ ውስጥ ይቅበር፤ ተስፋ ሊኖር ይችላልና። 30 ጕንጩን ለሚመታው ሰው ይስጥ፤ ውርደትንም ይጥገብ። כ ካፍ כ ካፍ 31 ጌታ ሰውን፣ ለዘላለም አይጥልምና፤ 32 መከራን ቢያመጣ እንኳ ይራራል፤ ታላቅ ፍቅሩ አይለወጥምና። 33 ሆነ ብሎ ችግርን፣ ወይም መከራን በሰው ልጆች ላይ አያመጣምና። ל ላሜድ ל ላሜድ 34 የምድሪቱ እስረኞች ሁሉ፣ በእግር ሲረገጡ፣ 35 በልዑል ፊት፣ ሰው መብቱ ሲነፈገው፣ 36 ሰው ፍትሕ ሲጓደልበት፣ ጌታ እንዲህ ዐይነቱን ነገር አያይምን? מ ሜም מ ሜም 37 ጌታ ካላዘዘ በቀር፣ ተናግሮ መፈጸም የሚችል ማን ነው? 38 ክፉም ሆነ መልካም ነገር፣ ከልዑል አፍ የሚወጣ አይደለምን? 39 ታዲያ ሕያው ሰው በኀጢአቱ ሲቀጣ፣ ስለ ምን ያጕረመርማል? נ ኑን נ ኑን 40 መንገዳችንን እንመርምር፤ እንፈትን፤ ወደ እግዚአብሔርም እንመለስ። 41 ልባችንን ከእጃችን ጋራ በሰማይ ወዳለው ወደ አምላካችን እናንሣ፤ እንዲህም እንበል፤ 42 “ዐምፀናል፤ ኀጢአትም ሠርተናል፤ አንተም ይቅር አላልኸንም። ס ሳሜክ ס ሳሜክ 43 “ራስህን በቍጣ ከደንህ፤ አሳደድኸንም፤ ያለ ርኅራኄም ገደልኸን። 44 ጸሎት እንዳያልፍ፣ ራስህን በደመና ሸፈንህ። 45 በአሕዛብ መካከል፣ አተላና ጥራጊ አደረግኸን። ע ዐዪን ע ዐዪን 46 “ጠላቶቻችን ሁሉ፣ አፋቸውን በእኛ ላይ ከፈቱ። 47 በጥፋትና በመፈራረስ፣ በችግርና በሽብር ተሠቃየን።” 48 የእንባ ጐርፍ ከዐይኔ ፈሰሰ፤ ሕዝቤ ዐልቋልና። פ ፌ פ ፌ 49 ያለ ዕረፍት፣ ያለ ማቋረጥ ዐይኖቼ እንባ ያፈስሳሉ፤ 50 እግዚአብሔር ከላይ፣ ከሰማይ እስኪያይ ድረስ። 51 በከተማዬ ባሉት ሴቶች ሁሉ ላይ የደረሰውን ማየቴ፣ ነፍሴን አስጨነቃት። צ ጻዲ צ ጻዲ 52 ያለ ምክንያት ጠላቶቼ የሆኑ፣ እንደ ወፍ ዐደኑኝ። 53 ሕይወቴን በጕድጓድ ውስጥ ሊያጠፉ ሞከሩ፣ ድንጋይም በላዬ አደረጉ። 54 ውሃ ሞልቶ በዐናቴ ላይ ፈሰሰ፤ ጠፍቻለሁ ብዬ አሰብሁ። ק ቆፍ ק ቆፍ 55 በጥልቁ ጕድጓድ ውስጥ ሳለሁ፣ እግዚአብሔር ሆይ፤ የአንተን ስም ጠራሁ። 56 ልመናዬን ሰምተሃል፤ “ርዳታም ፈልጌ ስጮኽ፣ ከመስማት ጆሮህን አትከልክል።” 57 በጠራሁህ ጊዜ ቀረብኸኝ፣ እንዲሁም፣ “አትፍራ” አልኸኝ። ר ሬሽ ר ሬሽ 58 ጌታ ሆይ፤ ለእኔ ተሟገትኽልኝ፤ ሕይወቴንም ተቤዠህ። 59 እግዚአብሔር ሆይ፤ በእኔ ላይ የተደረገውን ግፍ አየህ፤ ፍርዴን ፍረድልኝ! 60 በቀላቸውን ሁሉ፣ በእኔም ላይ ያሰቡትን ዐድማ አየህ። ש ሲን እና ሺን ש ሲን እና ሺን 61 እግዚአብሔር ሆይ፤ ስድባቸውን ሁሉ፣ በእኔ ላይ ያሰቡትን ዐድማ ሁሉ ሰማህ፤ 62 ይህም ቀኑን ሙሉ በእኔ ላይ፣ ጠላቶቼ የሚያውጠነጥኑትና የሚያንሾካሹኩት ነው። 63 ተመልከታቸው! ቆመውም ሆነ ተቀምጠው፣ በዘፈናቸው ይሣለቁብኛል። ת ታው ת ታው 64 እግዚአብሔር ሆይ፤ እጆቻቸው ላደረጉት፣ የሚገባውን መልሰህ ክፈላቸው። 65 በልባቸው ላይ መጋረጃን ዘርጋ፤ ርግማንህም በላያቸው ይሁን! 66 ከእግዚአብሔር ሰማያት በታች፣ በቍጣህ አሳድዳቸው፤ አጥፋቸውም። |
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.
Biblica, Inc.