ኢዮብ 32 - አዲሱ መደበኛ ትርጒምኤሊሁ 1 ኢዮብ በበኩሉ ራሱን እንደ ጻድቅ ቈጥሮ ስለ ነበር፣ እነዚህ ሦስት ሰዎች ለርሱ መልስ መስጠታቸውን ተዉ። 2 ከራም ወገን የሆነው፣ የቡዛዊው የባርክኤል ልጅ ኤሊሁ ግን ኢዮብ ከእግዚአብሔር ይልቅ ራሱን ጻድቅ ስላደረገ እጅግ ተቈጣው። 3 ሦስቱ የኢዮብ ጓደኞች በኢዮብ ላይ መፍረድ እንጂ፣ ነገሩን ሊያሳምኑት ስላልቻሉ፣ በእነርሱም ላይ ተቈጣ። 4 ኤሊሁ፣ ሌሎቹ በዕድሜ ይበልጡት ስለ ነበር ከእነርሱ ቀድሞ ለኢዮብ ሳይናገር ቈየ። 5 ነገር ግን ኤሊሁ እነዚህ ሦስቱ የሚሉትን ባጡ ጊዜ ቍጣው ነደደ። 6 ስለዚህ የቡዛዊው የባርክኤል ልጅ ኤሊሁ እንዲህ አለ፤ “እኔ በዕድሜ ታናሽ ነኝ፤ እናንተ ግን አዛውንቶች ናችሁ፤ ከዚህም የተነሣ የማውቀውን ለመናገር አልደፈርሁም፤ ፈርቼ ዝም አልሁ። 7 ‘ዕድሜ ይናገራል፤ ረዥም ዘመን ጥበብን ያስተምራል’ ብዬ ነበር። 8 ነገር ግን በሰው ያለው መንፈስ፣ ሁሉን ቻይ አምላክ እስትንፋስ፣ ማስተዋልን ይሰጣል። 9 ጠቢባን የሚሆኑት በዕድሜ የገፉ ብቻ አይደሉም፤ የሚያስተውሉም ሽማግሌዎች ብቻ አይደሉም። 10 “ስለዚህ፣ ‘ስሙኝ፣ እኔም የማውቀውን ልንገራችሁ’ እላለሁ። 11 እናንተ በምትነጋገሩበት ጊዜ ታገሥሁ፤ ቃላት እየመረጣችሁ ስትናገሩ፣ በጥሞና ሰማኋችሁ፤ 12 በሙሉ ልብ አደመጥኋችሁ፤ ነገር ግን ከእናንተ የኢዮብን ቃል ያስተባበለ ማንም የለም፤ ለንግግሩም አጸፋ የመለሰ አልተገኘም። 13 ‘እኛ ጥበብ አግኝተናል፤ ሰው ሳይሆን እግዚአብሔር ይርታው’ አትበሉ። 14 ኢዮብ ግን ቃሉን በእኔ ላይ አልሰነዘረም፤ እኔም እንደ እናንተ አነጋገር መልስ አልሰጠውም። 15 “እነርሱ ተስፋ ቈርጠው የሚሉት የላቸውም፤ የሚናገሩትም ጠፍቷቸዋል። 16 እንግዲህ እነርሱ መልስ ስላጡ፣ ጸጥ ብለውም ስለ ቆሙ፣ በትዕግሥት ልጠብቅን? 17 እኔም የምለው ይኖረኛል፤ የማውቀውንም እገልጣለሁ። 18 የምናገረው ሞልቶኛልና፤ በውስጤ ያለውም መንፈስ ገፋፍቶኛል። 19 ውስጤ እንደ ተከደነና መተንፈሻ እንዳጣ የወይን ጠጅ፣ ሊፈነዳ እንደ ተቃረበም አዲስ የወይን ጠጅ አቁማዳ ሆኗል። 20 ተናግሬ መተንፈስ አለብኝ፤ አፌንም ከፍቼ መልስ መስጠት ይገባኛል። 21 ለማንም አላደላም፤ ሰውንም አላቈላምጥም። 22 ማቈላመጥን ባውቅበትማ ኖሮ፣ ፈጣሪዬ ፈጥኖ ባጠፋኝ ነበር። |
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.
Biblica, Inc.