Biblia Todo Logo
在线圣经

- 广告 -

ኢሳይያስ 31 - አዲሱ መደበኛ ትርጒም


በግብጽ ለሚደገፉ ወዮላቸው

1 ወደ እስራኤል ቅዱስ ለማይመለከቱ፣ ከእግዚአብሔርም ርዳታን ለማይሹ፣ ነገር ግን፤ ለርዳታ ብለው ወደ ግብጽ ለሚወርዱ፣ በፈረሶች ለሚታመኑ፣ በሠረገሎቻቸው ብዛት፣ በፈረሶቻቸውም ታላቅ ብርታት ለሚመኩ ወዮላቸው!

2 እርሱም ግን ጠቢብ ነው፤ ጥፋትን ያመጣል፤ ቃሉን አያጥፍም። በክፉ አድራጊዎች ቤት ላይ፣ በደለኞችንም በሚረዱ ላይ ይነሣል።

3 ግብጻውያን ሰዎች እንጂ አምላክ አይደሉም፤ ፈረሶቻቸውም ሥጋ እንጂ መንፈስ አይደሉም፤ እግዚአብሔር እጁን ሲዘረጋ፣ ርዳታ ሰጪው ይሰናከላል፤ ተረጂውም ይወድቃል፤ ሁለቱም በአንድ ላይ ይጠፋሉ።

4 እግዚአብሔር እንዲህ ብሎኛል፤ “አንበሳ ወይም የአንበሳ ደቦል የሰበረውን ይዞ ሲያገሣ፣ ብዙ እረኞች ተጠራርተው ሲመጡበት፣ ጩኸታቸው እንደማያስፈራው፣ በድምፃቸውም እንደማይታወክ፣ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር፣ በጽዮን ተራራና በከፍታዎቿ ላይ ለውጊያ እንዲሁ ይወርዳል።

5 በዐናት ላይ እንደሚያንዣብቡ ወፎች፣ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ኢየሩሳሌምን እንዲሁ ይጋርዳታል፤ ይከልላታል፤ ይታደጋታል፤ በላይዋ ያልፋል፤ ያድናታልም።”

6 እናንተ እስራኤላውያን ሆይ፤ እጅግ ወዳመፃችሁበት ወደ እርሱ ተመለሱ።

7 በዚያ ቀን በኀጢአት የተሞላ እጃችሁ የሠራቸውን የወርቅና የብር ጣዖቶች ሁላችሁም ትጥላላችሁና።

8 “አሦር የሰው ባልሆነ ሰይፍ ይወድቃል፤ የሥጋ ለባሽ ያልሆነም ሰይፍ ይበላዋል። ከሰይፍ ፊት ይሸሻል፤ ጕልማሶቹም የግዳጅ ሥራ ይሠራሉ።

9 ጠንካራ ምሽጉ በሽብር ምክንያት ይወድቃል፤ መሪዎቹም የጦር ዐርማ ሲያዩ በድንጋጤ ይዋጣሉ” ይላል እሳቱ በጽዮን፣ ማንደጃውም በኢየሩሳሌም የሆነ እግዚአብሔር።

መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™

የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.

በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።

The Holy Bible, New Amharic Standard Version™

Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.

Used with permission. All rights reserved worldwide. 

Biblica, Inc.
跟着我们:



广告