Biblia Todo Logo
在线圣经

- 广告 -

ዕዝራ 3 - አዲሱ መደበኛ ትርጒም


መሠዊያው እንደ ገና ተሠራ

1 ሰባተኛው ወር በደረሰ ጊዜ፣ እስራኤላውያን በየከተሞቻቸው ሳሉ፣ ሕዝቡ እንደ አንድ ሰው ሆነው በኢየሩሳሌም ተሰበሰቡ።

2 ከዚያም የኢዮሴዴቅ ልጅ ኢያሱና ካህናት ዘመዶቹ እንዲሁም የሰላትያል ልጅ ዘሩባቤልና የሥራ ባልደረቦቹ፣ በእግዚአብሔር ሰው በሙሴ ሕግ በተጻፈው መሠረት የሚቃጠል መሥዋዕት ለማቅረብ፣ የእስራኤልን አምላክ መሠዊያ መሥራት ጀመሩ።

3 በዙሪያቸው ካሉት አሕዛብ የተነሣ ፍርሀት ቢያድርባቸውም፣ መሠዊያውን በቀድሞው መሠረት ላይ ሠሩ፤ በመሠዊያውም ላይ ጧትና ማታ የሚቀርበውን የሚቃጠል መሥዋዕት ለእግዚአብሔር አቀረቡ።

4 ከዚያም ለእያንዳንዱ ቀን እንደ ታዘዘው፣ በሚያስፈልገው ቍጥር ልክ የሚቃጠል መሥዋዕት በማቅረብ የዳስ በዓልን በተጻፈው መሠረት አከበሩ።

5 ከዚያም በኋላ መደበኛውን የሚቃጠል መሥዋዕት፣ የወር መባቻን መሥዋዕት፣ በተቀደሱት የእግዚአብሔር በዓላት የሚቀርበውን መሥዋዕትና የበጎ ፈቃድ ስጦታ ለእግዚአብሔር አቀረቡ።

6 የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መሠረት ገና ያልተጣለ ቢሆንም፣ በሰባተኛው ወር በመጀመሪያው ቀን ለእግዚአብሔር የሚቃጠል መሥዋዕት አቀረቡ።


ቤተ መቅደሱ እንደ ገና ተሠራ

7 ከዚያም ለድንጋይ ጠራቢዎችና ለየእጅ ጥበብ ባለሙያዎች ገንዘብ ሰጡ፤ ከፋርስ ንጉሥ ከቂሮስ በተፈቀደው መሠረት የዝግባ ዛፎች ከሊባኖስ ወደ ኢዮጴ በባሕር እንዲያመጡላቸው፣ ለሲዶናና ለጢሮስ ሰዎችም ምግብ፣ መጠጥና ዘይት ሰጡ።

8 ኢየሩሳሌም ወደሚገኘው ወደ እግዚአብሔር ቤት በደረሱ በሁለተኛው ዓመት በሁለተኛው ወር፣ የሰላትያል ልጅ ዘሩባቤልና የኢዮሴዴቅ ልጅ ኢያሱ እንዲሁም የቀሩት ወንድሞቻቸው (ካህናቱ፣ ሌዋውያኑ፣ ከምርኮ ወደ ኢየሩሳሌም የተመለሱት ሁሉ) ሃያ ዓመትና ከዚያም በላይ የሆናቸው ሌዋውያን የእግዚአብሔርን ቤት ሕንጻ ሥራ እንዲቈጣጠሩ ሾሟቸው፤ ሥራውንም ጀመሩ።

9 ኢያሱ፣ ወንዶች ልጆቹና ወንድሞቹ፣ የዮሖዳያ ዘሮች ቀድምኤልና ወንዶች ልጆቹ፣ የኤንሐዳድ ወንዶች ልጆች፣ ልጆቻቸውና ወንድሞቻቸው፣ ሌዋውያኑም ሁሉ የእግዚአብሔርን ቤት የሚሠሩትን ሰዎች ለመቈጣጠር በአንድ ላይ ሆኑ።

10 ግንበኞቹ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ መሠረት በጣሉ ጊዜ፣ ካህናቱ ልብሰ ተክህኗቸውን ለብሰውና መለከታቸውን ይዘው፣ ሌዋውያኑ የአሳፍ ልጆች ደግሞ ጸናጽል ይዘው፣ በእስራኤል ንጉሥ በዳዊት መመሪያ መሠረት እግዚአብሔርን ለመወደስ ስፍራቸውን ያዙ።

11 በውዳሴና በምስጋናም ለእግዚአብሔር እንዲህ ሲሉ ዘመሩ፤ “ቸር ነውና፤ ለእስራኤልም ምሕረቱ ለዘላለም ነውና።” የእግዚአብሔር ቤት መሠረት ስለ ተጣለ፣ ሕዝቡ ሁሉ በታላቅ ድምፅ እልል እያሉ፣ ለእግዚአብሔር ምስጋና አቀረቡ።

12 የቀድሞውን ቤተ መቅደስ ያዩ በዕድሜ የሸመገሉ ብዙ ካህናት፣ ሌዋውያንና የቤተ ሰብ አለቆች የዚህ ቤተ መቅደስ መሠረት ሲጣል ባዩ ጊዜ፣ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው አለቀሱ፤ ሌሎቹ ግን የደስታ ጩኸት አሰሙ።

13 የሕዝቡ ጩኸት ድብልቅልቅ ያለ ስለ ነበር፣ የደስታውን እልልታ ከልቅሶው ጩኸት መለየት የሚችል ማንም አልነበረም፤ ድምፁም ከሩቅ ይሰማ ነበር።

መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™

የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.

በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።

The Holy Bible, New Amharic Standard Version™

Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.

Used with permission. All rights reserved worldwide. 

Biblica, Inc.
跟着我们:



广告