ዘፀአት 21 - አዲሱ መደበኛ ትርጒም1 “በፊታቸው የምትደነግጋቸው ሥርዐቶች እነዚህ ናቸው፤ ዕብራዊ አገልጋይ 21፥2-11 ተጓ ምብ – ዘሌ 25፥39-55 2 “ዕብራዊ አገልጋይ ብትገዛ ስድስት ዓመት ያገልግልህ፤ በሰባተኛው ዓመት ግን ያለ ምንም ክፍያ በነጻ ይሂድ። 3 ብቻውን መጥቶ ከሆነ፣ ብቻውን በነጻ ይሂድ፤ ነገር ግን ሲመጣ ባለሚስት ከሆነ፣ እርሷ ዐብራው ትሂድ። 4 ጌታው ሚስት አጋብቶት ወንድ ወይም ሴት ልጅ ከወለደችለት፣ ሴትዮዋና ልጆቿ የጌታቸው ይሆናሉ፤ ሰውየው ብቻ በነጻ ይሂድ። 5 “ነገር ግን አገልጋዩ፤ ‘ጌታዬን፤ ሚስቴንና ልጆቼን እወድዳለሁ፤ ነጻ ሆኜ አልሄድም’ ቢል፣ 6 ጌታው ወደ ዳኞች ይውሰደው፤ ወደ በር ወይም ወደ በሩ መቃን ወስዶ ጆሮውን በወስፌ ይብሳው፤ ከዚያም ዕድሜ ዘመኑን የርሱ አገልጋይ ይሆናል። 7 “አንድ ሰው ሴት ልጁን አገልጋይ እንድትሆን ቢሸጣት፣ እንደ ወንዶቹ አገልጋዮች በነጻ መሸኘት የለባትም። 8 ለርሱ ትሆነው ዘንድ የመረጣትን ጌታዋን ደስ ባታሠኝ፣ በወጆ ይስደዳት፤ ለባዕዳን ይሸጣት ዘንድ መብት የለውም፤ ምክንያቱም ለርሷ ያለውን ታማኝነት አጓድሏልና። 9 ለወንድ ልጁ ትሆን ዘንድ መርጧት ከሆነ እንደ ራሱ ልጅ የሚገባትን መብት ይስጣት። 10 ሌላ ሴት ቢያገባ፣ ለመጀመሪያ ሚስቱ ምግቧን፣ ልብሷንና የጋብቻ መብቷን አይከልክላት። 11 እነዚህን ሦስት ነገሮች የማያሟላላት ቢሆን፣ ያለ አንዳች የገንዘብ ክፍያ በነጻ መሄድ ይኖርባታል። በሕይወት ላይ ለሚደርስ ጕዳት 12 “ሰውን ደብድቦ የገደለ ሞት ይገባዋል። 13 ሆኖም እግዚአብሔር ፈቅዶ ሰውየው ሳያውቅ በድንገት አድርጎት ከሆነ፣ እኔ ወደምወስነው ስፍራ ይሽሽ። 14 አንድ ሰው በተንኰል ሆነ ብሎ ሌላውን ቢገድል፣ ከመሠዊያዬ ተወስዶ ይገደል። 15 “አባቱን ወይም እናቱን የሚመታ ይገደል። 16 “አንዱ ሌላውን ጠልፎ የሸጠ ወይም በተያዘ ጊዜ ከእጁ ላይ የተገኘበት ይገደል። 17 “አባቱን ወይም እናቱን የሚሰድብ ይገደል። 18 “ሰዎች ተጣልተው አንዱ ሌላውን በድንጋይ ወይም በቡጢ ቢመታውና ተመቺው ሳይሞት በዐልጋ ላይ ቢውል፣ 19 በትሩንም ይዞ ደጅ ለደጅ የሚል ቢሆን፣ በዱላ የመታው ሰው አይጠየቅበትም፤ ሆኖም ለተጐጂው ሰው ለባከነበት ጊዜ ገንዘብ ይክፈል፤ ፈጽሞ እስኪድን ክትትል ያድርግለት። 20 “አንድ ሰው ወንድ ወይም ሴት ባሪያውን በዱላ ቢመታና ባሪያውም በዚህ የተነሣ ቢሞት መቀጣት አለበት፤ 21 ነገር ግን ከአንድ ወይም ከሁለት ቀን በኋላ ባሪያው ቢነሣ መቀጣት የለበትም፤ ባሪያው ንብረቱ ነውና። 22 “በጥል ላይ ያሉ ሰዎች ነፍሰ ጡር ሴት ቢመቱና እርሷም ያለጊዜዋ ብትወልድ፣ ጕዳቱም ለክፉ የማይሰጥ ቢሆን፣ ጕዳት ያደረሰባት ሰው የሴትየዋ ባል የጠየቀውንና ፈራጆቹ የፈቀዱትን ካሣ ሁሉ መክፈል አለበት። 23 ነገር ግን የከፋ ጕዳት ቢደርስ ሕይወት በሕይወት፣ 24 ዐይን በዐይን፣ ጥርስ በጥርስ፣ እጅ በእጅ፣ እግር በእግር፣ 25 ቃጠሎ በቃጠሎ፣ ቍስል በቍስል፣ ግርፋት በግርፋት ታስከፍላለህ። 26 “አንድ ሰው የወንድ ወይም የሴት አገልጋዩን ዐይን መትቶ ቢያጠፋ፣ ስለ ዐይን ካሳ አገልጋዩን ነጻ ይልቀቀው። 27 የወንድ ወይም የሴት አገልጋዩን ጥርስ ቢሰብር፣ ስለ ጥርስ ካሳ አገልጋዩን ነጻ ይልቀቀው። 28 “በሬ አንድን ወንድ ወይም ሴት ወግቶ ቢገድል፣ በሬው በድንጋይ ተወግሮ ይሙት፤ ሥጋውም አይበላ፤ ነገር ግን የበሬው ባለቤት በኀላፊነት አይጠየቅም። 29 ሆኖም በሬው የመውጋት ዐመል ያለበት ሆኖ ለባለቤቱም ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶት ሳለ በበረት ሳያስቀረው ቀርቶ አንድን ወንድ ወይም ሴት ቢገድል፣ በሬው በድንጋይ ይወገር፤ ባለቤቱም እንዲሁ ተወግሮ ይሙት። 30 ሆኖም ካሳ እንዲከፍል ከተጠየቀ፣ የተጠየቀውን ሁሉ በመክፈል ሕይወቱን ይዋጅ። 31 አንድ በሬ አንድን ወንድ ወይም ሴት ልጅ ቢወጋ በዚሁ ሕግ መሠረት ይፈጸም። 32 አንድ በሬ ወንድ ወይም ሴት ባሪያን ቢወጋ ባለቤቱ ሠላሳ የብር ሰቅል ለባሪያው ጌታ መክፈል አለበት፤ በሬውም በድንጋይ ይወገር። 33 “አንድ ሰው ጕድጓድን ከፍቶ ቢተው፣ ወይም ጕድጓድ ቈፍሮ ሳይከድነው ቢቀርና በሬ ወይም አህያ ቢገባበት፣ 34 የጕድጓዱ ባለቤት ኪሳራ ይክፈል፤ ለባለቤቱ መክፈል አለበት፤ የሞተውም እንስሳ ለርሱ ይሆናል። 35 “የአንድ ሰው በሬ የሌላውን ሰው በሬ ወግቶ ቢገድለው፣ በሕይወት ያለውን በሬ ሽጠው ገንዘቡንና የሞተውን እንስሳ እኩል ይካፈሉ። 36 ሆኖም በሬው የመዋጋት ዐመል ያለው መሆኑ ከታወቀ፣ ባለቤቱም በረት ሳይዘጋበት ቢቀር፣ ባለቤቱ በሬውን በበሬው ፈንታ ይክፈል፤ የሞተውም እንስሳ ለርሱ ይሆናል። |
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.
Biblica, Inc.