ሕዝቅኤል 42 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉምበቤተ መቅደሱ አጠገብ የተሠሩ ሁለት ሕንጻዎች 1 ከዚህም በኋላ ያ ሰው በውጭ በኩል ወደሚገኘው አደባባይ ወሰደኝ፤ ከባዶ ቦታ ፊት ለፊት እና በሰሜን በኩል ካለው ሕንጻ ትይዩ ወደነበሩት ክፍሎች አመጣኝ። 2 በሰሜን በኩል ያለው ሕንጻ ርዝመት መቶ ክንድ ሲሆን፥ ወርዱ ኀምሳ ክንድ ነበር። 3 ኻያ ክንድ የሆነው የውስጥ አደባባይ ታልፎ በውጪው አደባባይ ንጣፍ ትይዩ የተሠሩት ክፍሎች ከፎቅ ወደ ፎቅ እያደጉ ወደ ሦስተኛ ፎቅ ደርሰዋል። 4 ከክፍሎቹ ፊት ለፊት በውስጥ በኩል ዐሥር ክንድ ወርድና መቶ ክንድ ርዝመት ያለው መተላለፊያ ነበር፤ መግቢያዎቹም በስተ ሰሜን በኩል ነበሩ። 5 የሦስተኛው ፎቅ ክፍሎች ከሁለተኛውና ከምድር ቤቱ ክፍሎች የጠበቡ ናቸው። ይህም የሆነበት ምክንያት ፎቆቹ ከፍ ባሉ ቊጥር በረንዳዎቻቸው ሰፋ ስለሚሉና ክፍሎቹን ስለሚያጣብቡአቸው ነው። 6 እነርሱም በሦስት ፎቆች የተሠሩ ሲሆኑ እንደ ውጪው አደባባይ ሕንጻዎች ዐምዶች አልነበሩአቸውም። ስለዚህ የላይኛው ፎቅ ክፍሎች ከሁለተኛው ፎቅና ከምድር ቤቱ ክፍሎች ይልቅ ወደ ውስጥ ገባ ያሉ ነበሩ። 7 ከክፍሎቹ ፊት ለፊት ኀምሳ ክንድ ርዝመት ያለው በስተውጪው አደባባይ በኩል በክፍሎቹ ትይዩ አንድ ግንብ ነበር። 8 በውጪው አደባባይ በኩል ያሉት ክፍሎች ኀምሳ ክንድ ርዝመት ሲኖራቸው ከቤተ መቅደሱ ትይዩ ያሉት ክፍሎች ግን መቶ ክንድ ርዝመት ነበራቸው። 9 የታችኛዎቹ ክፍሎች በምሥራቅ በኩል ከወደ ውጪው አደባባይ መግቢያ ነበራቸው። 10 በስተ ደቡብ በኩል ደግሞ ከውጪው አደባባይ ግንብ ርዝመት ጐን ለጐን ከባዶ ቦታውና ከሕንጻው ፊት ለፊት ክፍሎች ነበሩ። 11 በክፍሎቹም ፊት ለፊት መተላለፊያ ነበር፤ ክፍሎቹ ልክ በሰሜን በኩል እንዳሉት ክፍሎች ርዝመትና ወርዳቸው፥ መውጫዎቻቸውና የበሮቻቸው አቀማመጥ ተመሳሳይ ነበር። 12 ስለዚህ በደቡብ በኩል ወዳሉት ክፍሎች መግቢያ በሮች የሚገባው በትይዩ በስተምሥራቅ ባለው ተመሳሳይ ግንብ መጨረሻ በሚገኘው መተላለፊያ በኩል ነው። 13 ያም ሰው እንዲህ አለኝ፦ “ከቤተ መቅደሱ ባዶ ቦታ ፊት ለፊት በሰሜንና በደቡብ ያሉት ክፍሎች የተቀደሱ ናቸው። የተቀደሱበት ምክንያት ወደ እግዚአብሔር የሚቀርቡት ካህናት የተቀደሱ ቊርባኖችን የሚበሉባቸው ቦታዎች ስለ ሆኑ ነው፤ ቦታዎቹም የተቀደሱ በመሆናቸው የእህል ቊርባን፥ የኃጢአት ማስተስረያ ቊርባንና ለበደል የሚቀርብ መሥዋዕትን ያኖሩባቸዋል። 14 ካህናቱ ወደተቀደሰው ቦታ ገብተው የሚያገለግሉባቸውን ልብሶች ከለበሱ በኋላ ያን ያገልግሎት ልብስ ሳያወልቁ ወደ ውጪው አደባባይ አይወጡም፤ ልብሶቹም የተቀደሱ ስለ ሆኑ ከተቀደሰው ቦታ ወጥተው ለሕዝብ ወደተፈቀደው ቦታ ከመድረሳቸው በፊት ሌላ ልብስ መልበስ ይኖርባቸዋል።” ቤተ መቅደሱ የተሠራበት ቦታ መጠን 15 ያ ሰው የቤተ መቅደሱን ውስጣዊ ክፍሎች ለክቶ ከጨረሰ በኋላ፥ በምሥራቁ የቅጽር በር በኩል ወደ ውጪ አወጣኝ፤ ከዚያም በኋላ የውጪውን ክልል ለካ። 16 የመለኪያውንም ዘንግ ወስዶ የምሥራቁን አቅጣጫ ሲለካ አምስት መቶ ክንድ ነው። 17 ከዚያም በኋላ በሰሜን በኩል በዘንጉ ሲለካ አምስት መቶ ክንድ ነው። 18 በደቡብ በኩልም ያው አምስት መቶ ክንድ ሆነ። 19 በምዕራቡ በኩል ሲለካ አምስት መቶ ክንድ ሆነ። 20 በተቀደሰውና በተራው ቦታ መካከል ለመለየት ቤተ መቅደሱን የሚከልለው ግንብ ርዝመቱ አምስት መቶ ክንድ፥ ወርዱ አምስት መቶ ክንድ ሆነ። |