ሕዝቅኤል 37 - አማርኛ አዲሱ መደበኛ ትርጉምየደረቁ አጥንቶች የተከማቹበት ሸለቆ 1 የእግዚአብሔር ኀይል በእኔ ላይ መጣ፤ የእርሱም መንፈስ እኔን ወስዶ ብዙ አጥንቶች በተከማቸበት ሸለቆ ውስጥ አኖረኝ፤ 2 በአጥንቶቹ መካከል አዙሮ አሳየኝ፤ በዚያም እጅግ የደረቁ በጣም ብዙ አጥንቶች ነበሩ። 3 እርሱም “የሰው ልጅ ሆይ! እነዚህ አጥንቶች ዳግመኛ ሕይወት የሚያገኙ ይመስልሃልን?” አለኝ። እኔም “ልዑል እግዚአብሔር ሆይ! ይህን የምታውቅ አንተ ብቻ ነህ” አልኩት። 4 እርሱም እንዲህ አለ፦ “ለእነዚህ አጥንቶች እንዲህ ብለህ ትንቢት ተናገር፦ እናንተ ደረቅ አጥንቶች የእግዚአብሔርን ቃል ስሙ፤ 5 እኔ ልዑል እግዚአብሔር የምላቸውን ሁሉ እንዲህ ብለህ ንገራቸው፦ ‘በውስጣችሁ እስትንፋስ በማስገባት እንደገና በሕይወት እንድትኖሩ አደርጋችኋለሁ። 6 ጅማትና ሥጋ በመስጠት ቆዳ አለብሳችኋለሁ፤ በውስጣችሁም እስትንፋስ አስገብቼ እንደገና በሕይወት እንድትኖሩ አደርጋችኋለሁ፤ በዚያን ጊዜ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን ታውቃላችሁ።’ ” 7 እኔም በታዘዝኩት መሠረት ትንቢት ተናገርኩ፤ መናገርም እንደ ጀመርኩ የመንኰሻኰሽ ድምፅ ሰማሁ፤ አጥንቶቹም እርስ በርሳቸው እየተገጣጠሙ መያያዝ ጀመሩ። 8 በመመልከት ላይ ሳለሁም አጥንቶቹ በጅማትና በሥጋ እንዲሁም በቈዳ ተሸፈኑ፤ እስትንፋስ ግን አልነበራቸውም። 9 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ “የሰው ልጅ ሆይ! ለነፋስ ትንቢት ተናገር፤ ነፋስ ከአራቱም ማእዘን መጥቶ ሕይወት እንዲያገኙ በእነዚህ በድኖች ላይ እንዲነፍስ ንገረው።” 10 እኔም በታዘዝኩት መሠረት ትንቢት ተናገርሁ፤ በእነርሱ ሁሉ ውስጥ እስትንፋስ ገባባቸው፤ ሁሉም ሕይወት አግኝተው ቆሙ፤ እጅግ ብዙ ሠራዊትም ሆኑ። 11 እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ “የሰው ልጅ ሆይ! የእስራኤል ሕዝብ እኮ ልክ እንደእነዚህ አጥንቶች ናቸው፤ እነርሱ ‘እነሆ፥ አጥንቶቻችን ደርቀዋል፤ ተስፋ ቈርጠናል፤ የእኛ ጉዳይ አልቆለታል’ ይላሉ። 12 ስለዚህም ለሕዝቤ ለእስራኤል ትንቢት ተናገር፤ እኔ ልዑል እግዚአብሔር መቃብራቸውን ከፍቼ እነርሱን በማውጣት ወደ እስራኤል ምድር የምመልሳቸው መሆኔን ንገራቸው። 13 ሕዝቤ የተቀበሩበትን መቃብር ሁሉ ከፍቼ በማወጣቸው ጊዜ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን ያውቃሉ። 14 እስትንፋሴን በእነርሱ ውስጥ አገባለሁ፤ በሕይወትም እንዲኖሩ አደርጋቸዋለሁ፤ በገዛ ምድራቸውም እንዲኖሩ አደርጋለሁ፤ ከዚያም በኋላ ይህን የተናገርኩና የማደርገውም እኔ እግዚአብሔር መሆኔን ያውቃሉ፤ እኔ እግዚአብሔር ይህን ተናግሬአለሁ።” የይሁዳና የእስራኤል በአንድ መንግሥት መጠቃለል 15 እግዚአብሔር እንዲህ ሲል ተናገረኝ፦ 16 “የሰው ልጅ ሆይ! አንድ በትር ወስደህ ‘በእርሱ ላይ ለይሁዳና ከእርሱ ጋር ለተባበሩ እስራኤላውያን’ ብለህ ጻፍ፤ ከዚያም ሌላ በትር ወስደህ በእርሱ ላይ ‘ለዮሴፍ ማለት ለኤፍሬምና ከእርሱ ጋር ለተባበሩ እስራኤላውያን’ ብለህ ጻፍ። 17 ከዚህ በኋላ በእጅህ አንድ ይሆኑ ዘንድ ሁለቱን በትሮች በአንድነት አገጣጥመህ ያዛቸው። 18 ሕዝብህም ይህ ምን መሆኑን እንድትነግራቸው በሚጠይቁህ ጊዜ፥ 19 ልዑል እግዚአብሔር እንዲህ ብሏል ብለህ ንገራቸው፦ በኤፍሬም እጅ ያለውን የዮሴፍን ከእነርሱ ጋር የተባበሩትን የእስራኤልን በትር ወስጄ አንድ በትር እንዲሆኑ ከይሁዳ በትር ጋር አጋጥማቸውና በእጄ አንድ ይሆናሉ። 20 “የጻፍክባቸውንም ሁለቱን በትሮች በእጅህ ይዘህ ሕዝቡ እንዲያዩአቸው አድርግ። 21 እኔ ልዑል እግዚአብሔር ሕዝቤን ሁሉ ከተበተኑባቸው ሕዝቦች መካከል በአንድነት ሰብስቤ ወደገዛ ምድራቸው መልሼ የማመጣቸው መሆኔን ንገራቸው። 22 በእስራኤል ምድርና በተራሮችዋ አንድ መንግሥት እንዲሆኑ አደርጋለሁ፤ ሁሉንም በአንድነት የሚያስተዳድር አንድ ንጉሥ ይኖራቸዋል፤ ዳግመኛ ሁለት ሕዝብ አይሆኑም፤ መንግሥታቸውም በሁለት አይከፈልም። 23 ዳግመኛ በጣዖቶቻቸው፥ በአጸያፊ ነገሮቻቸው፥ ወይም በሌሎች ኃጢአቶቻቸው ራሳቸውን አያረክሱም፤ ከወደቁበት ክሕደት አውጥቼ አነጻቸዋለሁ። በዚያን ጊዜ እነርሱ ሕዝቤ ይሆናሉ፤ እኔም አምላካቸው እሆናለሁ። 24 እንደ አገልጋዬ እንደ ዳዊት ያለ ንጉሥ ይኖራቸዋል፤ በአንድ መሪ ሥር ተጠቃለው ሕጎቼንና ሥርዓቴን በታማኝነት ይፈጽማሉ። 25 ለአገልጋዬ ለያዕቆብ በሰጠሁትና የቀድሞ አባቶቻቸውም በኖሩባት ምድር ይኖራሉ፤ በዚያችም ምድር እነርሱና ልጆቻቸው ዘሮቻቸውም ሳይቀሩ ለዘለዓለም ይኖራሉ፤ እንደ አገልጋዬ እንደ ዳዊት ያለ ንጉሥ በእነርሱ ላይ ለዘለዓለም ይነግሣል። 26 ከእነርሱ ጋር የሰላም ቃል ኪዳን እገባለሁ፤ ያም ቃል ኪዳን ዘለዓለማዊ ነው፤ እነርሱንም እንደገና መሥርቼ የሕዝቡን ቊጥር አበዛለሁ፤ ቤተ መቅደሴንም ለዘለዓለም ጸንቶ በሚቈይበት ስፍራ በምድራቸው አኖራለሁ። 27 እኔም በዚያ ከእነርሱ ጋር እኖራለሁ፤ እኔ አምላካቸው እሆናለሁ፤ እነርሱም ሕዝቤ ይሆናሉ። 28 ቤተ መቅደሴ በመካከላቸው ለዘለዓለም እንዲኖር በማደርግበት ጊዜ፤ ለእኔ እስራኤልን ለራሴ የተለየ ሕዝብ የማደርግ መሆኔን አሕዛብ ያውቃሉ።” |