ሩት 4 - መጽሐፍ ቅዱስ (የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት)ቦዔዝ ሩትን እንዳገባ 1 ቦዓዝም ወደ ከተማይቱ በር አደባባይ ወጥቶ በዚያ ተቀመጠ። እነሆም፥ ቦዔዝ ስለ እርሱ ይናገር የነበረው የቅርብ ዘመድ ሲያልፍ ቦዔዝ “አንተ ቀርበህ በዚህ ተቀመጥ፤” አለው። እርሱም ቀረብ ብሎ ተቀመጠ። 2 ቦዔዝም ከከተማይቱ ሽማግሌዎች ዐሥር ሰዎች ጠርቶ “በዚህ ተቀመጡ፤” አላቸው። 3 ቦዔዝም የቅርብ ዘመዱን “ከሞዓብ ምድር የተመለሰችው ኑኃሚን የወንድማችንን የአቤሜሌክን መሬት ትሸጣለች። 4 እኔም በዚህ በተቀመጡት በሕዝቤ ሽማግሌዎች ፊት እንድትገዛው አስታውቅህ ዘንድ አሰብሁ። መቤዠት ብትወድድ ተቤዥው፤ መቤዥት ባትወድድ ግን ከአንተ በቀር ሌላ ወራሽ የለምና፥ እኔም ከእንተ በኋላ ነኝና እንዳውቀው ንገረኝ፤” አለው። እርሱም “እቤዠዋለሁ፤” አለው። 5 ቦዔዝም “እርሻውን ከኑኃሚን እጅ በምትገዛበት ቀን፥ ለሞተው በርስቱ ስሙን እንድታስነሣለት ከምዋቹ ሚስት ከሞዓባዊቱ ከሩት ደግሞ ትገዛለህ፤” አለ። 6 የቅርብ ዘመዱም “የራሴን ርስት እንዳላበላሽ መቤዠት አልችልም፤ እኔ መቤዠቱን አልችልምና አንተ ከእኔ መቤዠቱን ውሰደው፤” አለ። 7 በጥንት ጊዜም፥ ማንም ቢሸጥ ቢለውጥም፥ ነገሩን ለማጽናት ሰው ጫማውን እንዲያወልቅ ለባልንጀራውም እንዲሰጠው በእስራኤል ዘንድ ልማድ ነበረ። ይህም በእስራኤል ምስክር ነበረ። 8 የቅርብ ዘመዱም ቦዔዝን “አንተ ግዛው” አለው፤ ጫማውንም አወለቀ። 9 ቦዔዝም ሽማግሌዎችንና ሕዝቡን ሁሉ “ለአቤሜሌክና ለኬሌዎን ለመሐሎንም የነበረውን ሁሉ ከኑኃሚን እጅ እንደ ገዛሁ እናንተ ዛሬ ምስክሮች ናችሁ። 10 ደግሞም የምዋቹ ስም ከወንድሞቹ መካከል ከአገርም ደጅ እንዳይጠፋ፥ የምዋቹን ስም በርስቱ ላይ እንዳስነሣ የመሐሎንን ሚስት ሞዓባዊቱን ሩትን ሚስት ትሆነኝ ዘንድ ወሰድሁአት፤ እናንተም ዛሬ ምስክሮች ናችሁ፤” አላቸው። 11 በከተማይቱ በር አደባባይም የነበሩ ሕዝብ ሁሉ ሽማግሌዎቹም “እኛ ምስክሮች ነን፤ እግዚአብሔር ይህችን ወደ ቤትህ የምትገባውን ሴት የእስራኤልን ቤት እንደ ሠሩ እንደ ሁለቱ እንደ ራሔልና እንደ ልያ ያድርጋት፤ አንተም በኤፍራታ ባለ ጠጋ ሁን፤ ስምህም በቤተ ልሔም ይጠራ። 12 ቤትህም እግዚአብሔር ከዚህች ቈንጆ ከሚስጥህ ዘር ትዕማር ለይሁዳ እንደ ወለደችው እንደ ፋሬስ ቤት ይሁን፤” አሉት። የዳዊት የትውልድ ሐረግ 13 ቦዔዝም ሩትን ወሰደ፤ ሚስትም ሆነችው፤ ደረስባትም፤ እግዚአብሔርም ፅንስ ሰጣት፤ ወንድ ልጅም ወለደች። 14 ሴቶችም ኑኃሚንን “ዛሬ ዋርሳ ያላሳጣሽ እግዚአብሔር ይባረክ፤ ስሙም በእስራኤል ይጠራ። 15 ከሰባትም ወንዶች ልጆች ይልቅ ለአንቺ ከምትሻል ከምትወድድሽ ምራት ተወልዶአልና ሰውነትሽን ያሳድሰዋል፤ በእርጅናሽም ይመገባሻል፤” አሉአት። 16 ኑኃሚንም ሕፃኑን ወሰደች አቀፈችውም፤ ሞግዚትም ሆነችው። 17 ሴቶችም ጎረቤቶችዋ፥ “ለኑኃሚን ወንድ ልጅ ተወለደላት፤” እያሉ ስም አወጡለት፤ ስሙንም ኢዮቤድ ብለው ጠሩት። እርሱም የዳዊት እባት የሆነው የእሴይ አባት ነው። 18 የፋሬስም ትውልድ ይህ ነው፤ ፋሬስ ኤስሮምን ወለደ፤ 19 ኤስሮምም አራምን ወለደ። አራምም አሚናዳብን ወለደ፤ 20 አሚናዳብም ነአሶንን ወለደ፤ ነአሶንም ሰልሞንን ወለደ፤ 21 ሰልሞንም ቦዔዝን ወለደ፤ 22 ቦዔዝም ኢዮቤድን ወለደ፤ ኢዮቤድም እሴይን ወለደ፤ እሴይም ዳዊትን ወለደ። |