መሳፍንት 10 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ቶላ 1 ከአቤሜሌክም በኋላ ከይሳኮር ነገድ የሆነ የአባቱ ወንድም ልጅ የፎሓ ልጅ ቶላ እስራኤልን ለማዳን ተነሣ፤ እርሱም በኤፍሬም ተራራ በሳምር ተቀምጦ ነበር። 2 እስራኤልንም ሃያ ሦስት ዓመት ገዛ፤ ሞተም፤ በሳምርም ተቀበረ። ኢያዕር 3 ከእርሱም በኋላ ገለዓዳዊዉ ኢያዕር ተነሣ፤ እስራኤልንም ሃያ ሁለት ዓመት ገዛ። 4 በሠላሳ ሁለት የአህያ ግልገሎች ይቀመጡ የነበሩ ሠላሳ ሁለት ልጆችም ነበሩት፤ ለእነርሱም እስከ ዛሬ ድረስ የኢያዕር መንደሮች የተባሉ በገለዓድ ምድር ያሉ ሠላሳ ሁለት ከተሞች ነበሩአቸው። 5 ኢያዕርም ሞተ፤ በራሞንም ተቀበረ። የእስራኤል ልጆች ስለ በደሉ በፍልስጥኤማውያንና በአሞናውያን እጅ እንደ ወደቁ 6 የእስራኤልም ልጆች በእግዚአብሔር ፊት እንደ ገና ክፉ ሥራ ሠሩ፤ በዓሊምንና አስታሮትን፥ የሶርያንም አማልክት፥ የሲዶናንም አማልክት፥ የሞዓብንም አማልክት፥ የአሞንንም ልጆች አማልክት፥ የፍልስጥኤማውያንንም አማልክት አመለኩ፤ እግዚአብሔርንም ተዉ፤ አላመለኩትምም። 7 እግዚአብሔርም በእስራኤል ላይ ፈጽሞ ተቈጣ፤ በፍልስጥኤማውያን እጅና በአሞን ልጆች እጅም አሳልፎ ሰጣቸው። 8 በዚያም ጊዜ የእስራኤልን ልጆች ሥቃይ አበዙባቸው፤ በዮርዳኖስ ማዶ በአሞሬዎናውያን ሀገር በገለዓድ ውስጥ ያሉትን የእስራኤልን ልጆች ሁሉ ዐሥራ ስምንት ዓመት አስጨነቁአቸው። 9 የአሞንም ልጆች ከይሁዳ፥ ከብንያምና ከኤፍሬም ቤት ጋር ደግሞ ሊዋጉ ዮርዳኖስን ተሻገሩ፤ እስራኤልም እጅግ ተጨነቁ። 10 የእስራኤልም ልጆች፥ “አንተን አምላካችንን ትተን በዓሊምን አምልከናልና ኀጢአት ሠርተናል” ብለው ወደ እግዚአብሔር ጮኹ። 11 እግዚአብሔርም የእስራኤልን ልጆች አላቸው፥ “ግብፃውያን፥ አሞሬዎናውያንም፥ የአሞንና የሞአብም ልጆች፥ ፍልስጥኤማውያንም፥ 12 ሲዶናውያንም፥ ምድያማውያንም፥ አማሌቃውያንም አላስጨነቋችሁምን? ወደ እኔም ጮኻችሁ፤ እኔም ከእጃቸው አዳንኋችሁ። 13 እናንተ ግን ተዋችሁኝ፤ ሌሎችንም አማልክት አመለካችሁ፤ ስለዚህም ደግሞ አላድናችሁም። 14 ሄዳችሁ ወደ መረጣችኋቸው አማልክት ጩኹ፤ እነርሱም በመከራችሁ ጊዜ ያድኑአችሁ።” 15 የእስራኤልም ልጆች እግዚአብሔርን፥ “እኛ ኀጢአትን ሠርተናል፤ አንተ በፊትህ ደስ የሚያሰኝህን አድርግብን፤ ዛሬ ግን እባክህ አድነን” አሉት። 16 ሌሎችንም አማልክት ከመካከላቸው አስወገዱ፤ እግዚአብሔርንም ብቻ አመለኩ፤ ደስም አሰኙት፤ የእስራኤልም ልጆች ከሥቃይ የተነሣ አእምሮአቸውን አጥተው ነበር። 17 የአሞንም ልጆች ወጥተው በገለዓድ ሰፈሩ። የእስራኤልም ልጆች ተሰብስበው በመሴፋ ሰፈሩ። 18 የገለዓድ ሕዝብ አለቆችም እርስ በርሳቸው፥ “ከአሞን ልጆች ጋር መዋጋትን የሚጀምር ማን ነው? እርሱ በገለዓድ ሰዎች ሁሉ ላይ አለቃ ይሆናል” አሉ። |