ኢዮብ 20 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የሶፋር ሁለተኛ ንግግር 1 አሜናዊውም ሶፋር መለሰ፤ እንዲህም አለ፦ 2 “እንደዚህ እንደምትመልስ አልጠረጠርሁህም ነበር፤ በዕውቀትም ከእኔ አትሻልም። 3 የትምህርቴን ጥበብ ልንገርህ፤ ስማኝ፤ የማስተዋሌም መንፈስ ይመልስልኛል። 4 ሰው በምድር ላይ ከተፈጠረ፥ ከድሮ ዘመን ጀምሮ፥ በአንተስ ዘመን እንደዚህ ያለ ነገር ታውቃለህን? 5 የኀጢኣተኞች ደስታ ታላቅ ሰልፍ ነው፥ የዝንጉዎችም ደስታ ጥፋት ነው። 6 መባው ወደ ሰማይ ቢወጣ፥ መሥዋዕቱም እስከ ደመና ቢደርስ፥ 7 እነሆ ተደላድያለሁ በሚልበት ጊዜ ለዘለዓለም ይጠፋል። የሚያውቁትም ወዴት ነው? ይላሉ። 8 እንደ ሕልም ይበርራል፤ እርሱም አይገኝም፤ ሲነጋም እንደማይታወቅ እንደ ሌሊት ራእይ ይሰደዳል። 9 ዐይን አየችው፤ ነገር ግን ዳግመኛ አታየውም፤ ስፍራውንም ከእንግዲህ ወዲህ አያውቀውም። 10 የተዋረዱ ሰዎች ልጆቹን ያጠፋሉ፤ እጆቹም የኀዘን እሳትን ያቀጣጥላሉ። 11 ጭንቀት በአጥንቶቹ ሞልቶአል፤ ነገር ግን ሕማሙ ከእርሱ ጋር በመሬት ውስጥ ይተኛል። 12 “ክፋት በአፉ ውስጥ ብትጣፍጠው፤ ከምላሱም በታች ቢሰውራት፥ 13 ቢጠብቃትም፥ ባይተዋትም፤ በጕሮሮውም መካከል ቢይዛት፥ መብሉ በአንጀቱ ውስጥ ይገላበጣል፤ 14 ፈጽሞ ራሱን መርዳት አይችልም። የእፉኝትም መርዝ ከከንፈሩ በታች አለ። 15 በዐመፅ የሚሰበሰብ ሀብትም ይጠፋል፤ የሞት መልአክም ከቤቱ ውስጥ እያዳፋ ያወጣዋል። 16 የእባብን መርዝ ይጠባል፤ የእፉኝትም ምላስ ይገድለዋል። 17 የመንጋዎቹንም ጥጆች፥ የማሩንና የቅቤውንም ፈሳሽ አይመለከትም። 18 ለማይቀምሰው፥ ለማይታኘክና ለማይዋጥ ሀብት በከንቱ ይደክማል። 19 የደካሞችን ቤቶች አፍርሶአልና፤ ያልሠራውንም ቤት በዝብዞአልና። 20 ለንብረቱ ጥበቃ የለውም፤ የወደደውንም ነገር አያገኝም። 21 ለሀብቱ ትርፍ የለውም፤ ስለዚህ በረከቱ አትከናወንለትም። 22 በጠገበ ጊዜ ይጨነቃል፤ መከራም ሁሉ ያገኘዋል። 23 “ሆዱን ቢያጠግብ፥ የመዓት መቅሠፍት ይጨመርበታል፤ የሕማሙም ሥቃይ ይጸናበታል። 24 ከሰይፍም ኀይል አያመልጥም፤ የናስም ቀስት ይወጋዋል። 25 ቀስቱም በሥጋው ውስጥ ያልፋል። ክፉም ነገር በሰውነቱ ይመላለሳል፤ ፍርሀትም ይወድቅበታል። 26 ጨለማ ሁሉ ይጠብቀዋል፤ ዕፍ የማይባል እሳትም ይበላዋል፤ እንግዳም ቤቱን ያጠቃዋል። 27 ሰማይ ኀጢኣቱን ይገልጥበታል፤ ምድርም በእርሱ ላይ ትነሣለች። 28 ጥፋትም ቤቱን ወደ ፍጻሜ ያመጣታል። የቍጣ ቀንም ትመጣበታለች። 29 ከእግዚአብሔር ዘንድ የኀጢአተኛ ሰው እድል ፋንታው፥ ከሚያየው ከፈጣሪውም የተመደበ ርስቱ ይህ ነው።” |