ኢዮብ 18 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የበልዳዶስ ንግግር 1 አውኬናዊው በልዳዶስ መለሰ እንዲህም አለ፦ 2 “ዝም የማትለው እስከ መቼ ነው? እኛም እንድንነግርህ ታገሥ። 3 ስለ ምንስ እንደ እንስሳ በፊትህ ዝም አልን? 4 መከራው ይገባሃል፤ አንተስ የሞትህ እንደ ሆነ ምንድን ነው? ከሰማይ በታች ምድር ስለ አንተ ባድማ ትሆናለችን? ወይስ ተራራዎች ከመሠረታቸው ይናወጣሉን? 5 “የኀጢኣተኞች መብራት ይጠፋል፥ ነበልባላቸውም ብልጭ አይልም። 6 ብርሃኑ በድንኳኑ ውስጥ ይጨልማል፤ መብራቱም በላዩ ይጠፋል። 7 የተዋረዱ ሰዎች ንብረቱን ይወስዳሉ፤ ምክሩም ትጥለዋለች። 8 እግሩ በወጥመድ ትያዛለች፤ በመረብም ትታሠራለች፤ 9 አሽክላዎች በላዩ ይመጣሉ፤ የተጠሙትም በእርሱ ይበረታሉ፤ 10 በምድር ላይ የሸምቀቆ ገመዱ ተሰውራለች፤ የሚጐትተውም በመንገዱ ላይ ነው። 11 መከራ በዙሪያው ታጠፋዋለች፤ ብዙ ጠላቶችም ከእግሩ በታች ይመጣሉ። 12 ኀይሉ በራብ ትደክማለች። አስጨናቂ መቅሠፍትም ተዘጋጅቶለታል። 13 ጭኖቹ ይበሰብሳሉ። ሞትም መልካም ሕዋሶቹን ይበላል። 14 ጤንነት ከሥጋው ትርቃለች። መከራው ትጸናለች፤ እግዚአብሔርም ይበቀለዋል። 15 በሌሊት በድንኳኑ ውስጥ ለእርሱ የማይሆነው ይኖራል፤ የእርሱም መልካም ነገር በዲን ይበተናል። 16 ሥሩ ከበታቹ ይደርቃል፤ ፍሬውም ከላዩ ይረግፋል። 17 መታሰቢያውም ከምድር ይጠፋል፤ በምድርም ስም አይቀርለትም። 18 ከብርሃን ወደ ጨለማ አርቀው ያፈልሱታል። 19 ከሕዝቡ መካከል የሚራራለት የለም፤ ቤቱ ከሰማይ በታች አይቀርለትም። 20 ነገር ግን ባዕድ በንብረቱ ላይ ተድላ ያደርጋል፤ ድሃው በእርሱ ያጕረመርማል። ፊተኞቹም ይደነቃሉ። 21 የኀጢኣተኞች ቤት እንዲህ ነው፤ እግዚአብሔርንም የማያውቁ ሰዎች ስፍራ ይህ ነው።” |