ኢዮብ 13 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)1 “እነሆ፥ ይህን ሁሉ ዐይኔ አየች፤ ጆሮየም ሰማች። 2 እናንተ የምታውቁትን እኔ ደግሞ አውቃለሁ፤ ከእናንተም የምሰንፍ አይደለሁም። 3 ነገር ግን ለእግዚአብሔር እናገራለሁ፤ ከፈቀደም በፊቱ እዋቀሳለሁ። 4 እናንተ ግን የዐመፅ ባለ መድኀኒቶች፥ ሁላችሁም የክፋት ፈዋሾች ናችሁ። 5 ላዳምጣችሁ አይገባኝም፥ ጥበብ ከእናንተ ጠፍታለችና። 6 “አሁን የአፌን ክርክር ስሙ፥ የከንፈሬንም ፍርድ አድምጡ። 7 በውኑ በእግዚአብሔር ፊት የምትናገሩ አይደላችሁምን? በፊቱ ሽንገላን ታወራላችሁን? 8 ከእርሱ ወደ ኋላ ትመለሳላችሁን? እስኪ ራሳችሁ ፍረዱ። 9 እርሱ ቢመረምራችሁ መልካም ነው፥ ይህን ሁሉ በኀይላችሁ ስታደርጉ ራሳችሁን ከእርሱ ጋር አንድ ታደርጋላችሁና። 10 በስውር ለሰው ፊት ብታደሉ ዘለፋ ይዘልፋችኋል። 11 ጥንቱን ኀይሉ አያስፈራችሁምን? ግርማስ ከእርሱ ዘንድ አይወድቅባችሁምን? 12 ምሳሌያችሁ እንደ አመድ ዐላፊ ነው፤ ሥጋችሁም እንደ ትቢያ ነው። 13 ዝም በሉ፤ እናገርም ዘንድ ተዉኝ፤ ከቍጣዬም ልረፍ። 14 ሥጋዬን በጥርሴ እይዛለሁ፤ ሕይወቴንም በእጄ አጥብቄ አኖራታለሁ። 15 እነሆ፥ ኀያሉ እጁን በእኔ ላይ ቢጭን፥ እርሱ እንደ ጀመረ እናገራለሁ፥ በፊቱም እዋቀሳለሁ። 16 ዝንጉ ሰው በፊቱ አይገባምና እርሱ መድኀኒት ይሆንልኛል። 17 ነገሬን ስሙ ስሙ፥ እኔ በጆሮአችሁ እነግራችኋለሁና። 18 እነሆ፥ ወደ ፍርዴ ቀርቤአለሁ። ጽድቄም እንደምትገለጥ አውቃለሁ። 19 አሁን ፈጽሜ ዝም እል ዘንድ፥ ከእኔ ጋር የሚፋረድ ማን ነው? 20 “ነገር ግን ሁለት ነገርን ስጠኝ፤ የዚያን ጊዜ ከፊትህ አልሰወርም፤ 21 እጅህን ከእኔ አርቅ፤ ግርማህም አታስደንግጠኝ። 22 ከዚህም በኋላ ትጠራኛለህ፥ እኔም እመልስልሃለሁ። ወይም አንተ ተናገር፥ አኔም እመልስልሃለሁ። 23 ኀጢአቶችና በደሌ ምን ያህል ናቸው? ምን ያህል እንደ ሆኑ አስታውቀኝ። 24 “ፊትህን ከእኔ የሰወርህ፥ እንደ ጠላትህም የቈጠርኸኝ ስለምን ነው? 25 በነፋስ እንደ ረገፈ ቅጠል ታፍሰኛለህን? ወይስ ነፋስ እንደሚወስደው ዕብቅ ታሳድደኛለህን? 26 ክፉ ነገርን ጽፈህብኛልና፤ የልጅነቴንም ኀጢአት ተቈጣጥረህ አስታጥቀኸኛልና። 27 እግሮችንም በድጥ አሰነካከልህ፥ ሥራዬንም ሁሉ መርምረሃል፤ እግሬም በቆመች ጊዜ ተውኸኝ። 28 እኔ እንደ አረጀ ረዋት፥ ብልም እንደሚበላው ልብስ ነኝ። |