ኢሳይያስ 17 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ሶርያና እስራኤል እንደሚቀጡ 1 ስለ ደማስቆ የተነገረ ቃል። “እነሆ፥ ደማስቆ ከከተሞች መካከል ተለይታ ትጠፋለች፤ ትፈርሳለችም። 2 ለዘለዓለም የተፈታች ትሆናለች፤ ለመንጋ ማሰማርያም ትሆናለች፤ የሚያሳድዳቸውም የለም። 3 ኤፍሬም የሚጠጋበት ምሽግ አይኖርም፤ ከእንግዲህም ወዲያ ንጉሥ በደማስቆ አይነግሥም። የሶርያ ቅሬታ ሆይ፥ ከእስራኤል ልጆች ከክብራቸው የምትሻል አይደለህም” ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር። 4 “በዚያም ቀን እንዲህ ይሆናል፤ የያዕቆብ ክብር ይደክማል፤ የሚበዛ የክብሩ ብልጽግናም ይነዋወጣል። 5 አጫጅ የቆመውን እህል ሰብስቦ ዛላውን እንደሚያጭድ ይሆናል፤ በሸለቆ እሸትን እንደሚሰበስብም እንዲሁ ይሆናል። 6 ወይራ በተመታ ጊዜ ሁለት ወይም ሦስት ፍሬ በራሱ ላይ እንደሚቀር፥ አራት ወይም አምስት በዛፊቱ ጫፍ እንደሚገኝ፥ በእርሱ ዘንድ ቃርሚያ ይቀራል” ይላል የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር። 7 በዚያም ቀን ሰው በፈጣሪው ይታመናል፤ ዐይኖቹም ወደ እስራኤል ቅዱስ ያያሉ። 8 በጣዖታቸውና ጣቶቻቸው በሠሩአቸው የእጃቸው ሥራዎች አይተማመኑም፤ ለርኵሰታቸውም ዛፎችን አይቈርጡም። 9 በዚያም ቀን በእስራኤል ልጆች ፊት የአሞራውያንና የኤዌዎያውያን ከተሞች እንደ ተፈቱ፥ እንዲሁ ከተሞችህ ይፈታሉ፤ ባድማም ይሆናሉ። 10 አዳኝህ እግዚአብሔርን ትተኸዋልና፥ ረዳትህ እግዚአብሔርንም አላስብኸውም፤ ስለዚህ የሐሰትን ተክል ተክለሃል፤ የሐሣርንም ዘር ዘርተሃል። 11 ተክልን በተከልህበት ቀን ትበድላለህ፤ የዘራኸውም በበነጋው በምታወርስበት ቀን ይበቅላል፤ አባትም ለልጁ እንደሚያወርስ አንተም ለልጆችህ ታወርሳለህ። 12 እንደ ውኃ ለሞሉ፥ ከተራራ በመከታተል እንደሚወርድ የውኃ ፈሳሽ ለሆኑም ብዙዎች አሕዛብ ወዮላቸው! 13 ብዙዎች አሕዛብ እንደ ብዙ ውኃ ናቸው፤ ከፏፏቴ ውስጥ በኀይል እንደሚወርድ እንደ ብዙ ውኃ ፈሳሽ ይጮኻሉ፤ ያጠፉታልም፤ እነርሱም ከሩቅ ይወርዳሉ፤ በተራራም ላይ እንዳለ እብቅ፥ በነፋስ ፊት ዐውሎ ነፋስ እንደሚያዞረው እንደ መንኰራኵር ትቢያም ይበተናሉ። 14 በመሸም ጊዜ ሳይነጋ ያለቅሳሉ፤ ያንጊዜም የይሁዳ ወገኖች “ይህ የወራሾች ርስት ነው፤ የበዘበዙንም ዕድል ፋንታ ይህ ነው” ይላሉ። |