ዘፀአት 27 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የመሠውያው አሠራር ( ዘፀ. 38፥1-7 ) 1 “ርዝመቱ አምስት ክንድ፥ ወርዱም አምስት ክንድ መሠዊያን ከማይነቅዝ ዕንጨት አድርግ፤ አራት ማዕዘንም ይሁን፤ ከፍታውም ሦስት ክንድ ይሁን። 2 በአራቱም ማዕዘን ቀንዶችን ታደርጋለህ፤ ቀንዶቹ ሥረ-ወጥ ይሁኑ፤ በናስም ለብጣቸው። 3 ለመሠዊያው ክዳን ሥራለት፤ መሸፈኛውን፥ ጽዋዎቹን፥ የሥጋ ሜንጦዎቹን፥ የእሳት መጫሪያዎቹንም አድርግ። ዕቃውንም ሁሉ ከናስ አድርግ። 4 ለመሠዊያውም እንደ መረብ ሆኖ የተሠራ የናስ መከታ አድርግለት፤ ለመከታውም አራት የናስ ቀለበት በአራት ማዕዘኑ አድርግለት። 5 መከታውም እስከ መሠዊያው እኩሌታ ይደርስ ዘንድ ከመሠዊያው እርከን በታች አኑረው። 6 ለመሠዊያውም ከማይነቅዝ ዕንጨት መሎጊያዎችን ሠርተህ በናስ ለብጣቸው፤ መሎጊያዎቹም በቀለበቶች ውስጥ ይግቡ፤ 7 መሠዊያውንም ስትሸከሙ መሎጊያዎቹ በመሠዊያው በሁለት ወገን ይሁኑ። 8 ሰሌዳውም ፍልፍል ይሁን፤ በተራራው እንዳሳየሁህ ምሳሌ እንዲሁ አድርግ። የቤተ እግዚአብሔር አደባባይ ( ዘፀ. 38፥9-20 ) 9 “ለድንኳኑም አደባባይ ሥራ፤ ከጥሩ በፍታ የተሠሩ የአደባባዩ መጋረጃዎችም በደቡብ በኩል ይሁኑ። የአንዱም ወገን ርዝመት መቶ ክንድ ይሁን፤ 10 ከናስ የተሠሩ ሃያ ምሰሶዎችና ሃያ እግሮች ይሁኑለት፤ የምሰሶዎቹም ኩላቦችና ዘንጎች የብር ይሁኑ። 11 እንዲሁም በሰሜን ወገን መቶ ክንድ ርዝመት ያላቸው መጋረጃዎች፥ ከናስ የተሠሩ ሃያ ምሰሶዎች፥ ሃያም እግሮች ይሁኑ፤ ለምሰሶዎችም በብር የተለበጡ ኩላቦችና ዘንጎች ይሁኑ። 12 በምዕራብም ወገን ለአደባባዩ ስፋት አምሳ ክንድ ርዝመት ያላቸው መጋረጃዎች፥ ዐሥርም ምሰሶዎች፥ ዐሥርም እግሮች ይሁኑለት። 13 በምሥራቅም ወገን የአደባባዩ ስፋት አምሳ ክንድ ይሁን፤ ምሰሶዎችም ዐሥር፥ እግሮቹም ዐሥር ይሁኑ። 14 በአንድ ወገን የመጋረጃዎቹ ርዝመት ዐሥራ አምስት ክንድ ይሁን፤ ምሰሶዎቹም ሦስት፥ እግሮቹም ሦስት ይሁኑ። 15 በሌላውም ወገን የመጋረጃዎቹ ርዝመት ዐሥራ አምስት ክንድ ይሆናል፤ ምሰሶዎቹም ሦስት፥ እግሮቹም ሦስት ይሁኑ። 16 ለአደባባዩ ደጅም ከሰማያዊ፥ ከሐምራዊም ከቀይም ግምጃ ከጥሩ በፍታም በጥልፍ አሠራር የተሠራ ሃያ ክንድ መጋረጃ ይሆናል፤ ምሰሶዎቹም አራት፥ እግሮቹም አራት ይሁኑ። 17 በዙሪያውም ያሉ የአደባባዩ ምሰሶዎች ሁሉ በብር የተለበጡ ይሁኑ፤ የብርም ክባሶች፥ የናስም እግሮች ይሁኑላቸው። 18 የአደባባዩ ርዝመት በየገጹ መቶ ክንድ፥ ስፋቱም በየገጹ አምሳ ክንድ ይሁን፤ የመጋረጃውም ከፍታ አምስት ክንድ ይሁን፤ መጋረጃውም ከጥሩ በፍታ፥ እግሮቹም ከናስ የተሠሩ ይሁኑ። 19 ለማገልገል ሁሉ የድንኳን ዕቃ ሁሉ፥ አውታሮቹ ካስማዎቹም ሁሉ፤ የአደባባዩም ካስማዎች ሁሉ የናስ ይሁኑ። የመብራቱ ዘይት ( ዘሌ. 24፥1-4 ) 20 “አንተም መብራቱን ሁል ጊዜ ያበሩት ዘንድ ለመብራት ተወቅጦ የተጠለለ ጥሩ የወይራ ዘይት እንዲያመጡልህ የእስራኤልን ልጆች እዘዛቸው። 21 በምስክሩ ድንኳን ውስጥ በቃል ኪዳኑ ታቦት ፊት ካለው መጋረጃ ውጭ አሮንና ልጆቹ ከማታ እስከ ማለዳ ድረስ በእግዚአብሔር ፊት ያብሩት፤ በእስራኤል ልጆች ዘንድ ለልጅ ልጃቸው የዘለዓለም ሥርዐት ይሁን። |