2 ዜና መዋዕል 22 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የአካዝያስ ዘመነ መንግሥት ( 2ነገ. 8፥25-29 ፤ 9፥21-28 ) 1 በኢየሩሳሌምም የነበሩት ታናሹን ልጁን አካዝያስን በእርሱ ፋንታ አነገሡት። የመጣባቸው የዓረብና የአሊማዞን የሽፍቶች ጭፍራ የእርሱን ታላቆች ወንድሞች ገድለዋቸው ነበርና የይሁዳ ንጉሥ የኢዮራም ልጅ አካዝያስ ነገሠ። 2 አካዝያስም መንገሥ በጀመረ ጊዜ ዕድሜው ሃያ ሁለት ዓመት ነበረ፥ በኢየሩሳሌምም አንድ ዓመት ነገሠ፤ እናቱም ጎቶልያ የተባለች የዘንበሪ ልጅ ነበረች። 3 እናቱም ክፉ እንዲያደርግ ትመክረው ነበርና እርሱ ደግሞ በአክዓብ ቤት መንገድ ሄደ። 4 ከአባቱም ሞት በኋላ የአክዓብ ቤት እንዳደረገ በእግዚአብሔር ፊት ክፉ አደረገ፤ ያጠፉት ዘንድ መካሪዎች ነበሩትና። 5 በምክራቸውም ሄደ፤ ከእስራኤልም ንጉሥ ከአክዓብ ልጅ ከኢዮራም ጋር የሶርያን ንጉሥ አዛሄልን በሬማት ዘገለዓድ ሊዋጋ ሄደ፤ ሶርያውያንም ኢዮራምን አቈሰሉት። 6 ከሶርያም ንጉሥ ከአዛሄል ጋር በተዋጋ ጊዜ ሶርያውያን በሬማት ያቈሰሉትን ቍስል ይታከም ዘንድ ወደ ኢይዝራኤል ተመለሰ፤ ታምሞም ነበርና የይሁዳ ንጉሥ የኢዮራም ልጅ አካዝያስ የአክዓብን ልጅ ኢዮራምን ያይ ዘንድ ወደ ኢይዝራኤል ወረደ። 7 ወደ ኢዮራም በመምጣቱም የአካዝያስ ጥፋት ከእግዚአብሔር ሆነ፤ በመጣም ጊዜ ከኢዮራም ጋር እግዚአብሔር የአክዓብን ቤት ያጠፋ ዘንድ ወደ ቀባው ወደ ናሚሲ ልጅ ወደ ኢዩ ወጣ። 8 ኢዩም የአክዓብን ቤት ይበቀል ዘንድ የይሁዳን መሳፍንትና አካዝያስን ያገለግሉ የነበሩትን የአካዝያስን ወንድሞች አግኝቶ ገደላቸው። 9 አካዝያስንም ፈለገው፤ በሰማርያም እየታከመ ሳለ አገኙት፤ ወደ ኢዩም አመጡት፤ እርሱም ገደለው፦ እነርሱም፥ “በፍጹም ልብ እግዚአብሔርን የፈለገው የኢዮሣፍጥ ልጅ ነው” ብለው ቀበሩት። ከአካዝያስም ቤት ማንም መንግሥትን ይይዝ ዘንድ የሚችል አልነበረም። የአካዝያስ እናት ጎቶልያ ( 2ነገ. 11፥1-3 ) 10 የአካዝያስም እናት ጎቶልያ ልጅዋ እንደ ሞተ ባየች ጊዜ ተነሥታ የይሁዳን ቤተ መንግሥት ዘር ሁሉ አጠፋች። 11 የንጉሡ ልጅ ዮሳቤት ግን ከተገደሉት ከንጉሡ ልጆች መካከል የአካዝያስን ልጅ ኢዮአስን ሰርቃ ወሰደች፤ እርሱንና ሞግዚቱን በእልፍኝ ውስጥ አኖረቻቸው፤ የንጉሡ የኢዮራም ልጅ የአካዝያስ እኅት የካህኑ የዮዳሄ ሚስት ዮሳቤት ከጎቶልያ ፊት ሸሸገችው፤ እርስዋም አልገደለችውም። 12 ከእርስዋም ጋር በእግዚአብሔር ቤት ተሸሽጎ ስድስት ዓመት ያህል ተቀመጠ፤ ጎቶልያም በምድር ላይ ነገሠች። |