2 ዜና መዋዕል 16 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)ይሁዳና እስራኤል እንደ ተዋጉ ( 1ነገ. 15፥17-22 ) 1 አሳ በነገሠ በሠላሳ ስድስተኛው ዓመት የእስራኤል ንጉሥ ባኦስ በይሁዳ ላይ ዘመተ፥ ወደ ይሁዳም ንጉሥ ወደ አሳ ማንም መውጣትና መግባት እንዳይችል ራማን ሠራት። 2 አሳም ከእግዚአብሔር ቤትና ከንጉሥ ቤት መዝገብ ብርና ወርቅ ወስዶ፦ በደማስቆ ወደ ተቀመጠው ወደ ሶርያ ንጉሥ ወደ ወልደ አዴር ላከ። እንዲህም አለው፦ 3 “በአባቴና በአባትህ መካከል እንደ ነበረው ቃል ኪዳን በእኔና በአንተ መካከል አድርግ፤ የእስራኤል ንጉሥ ባኦስ ከእኔ ዘንድ እንዲርቅ መጥተህ ትወጋው ዘንድ እነሆ፥ ወርቅና ብር ልኬልሃለሁ።” 4 ወልደ አዴርም ንጉሡን አሳን ሰማው፤ የሠራዊቱንም አለቆች በእስራኤል ከተሞች ላይ ሰደደ፤ እነርሱም አእዮንንና ዳንን፥ አቤልማይምንና የንፍታሌምንም አውራጃ ከተሞች ሁሉ መቱ። 5 ባኦስም በሰማ ጊዜ ራማን መሥራት ተወ፤ ሥራውንም አቋረጠ። 6 የይሁዳ ንጉሥ አሳም የይሁዳን ሰዎች ሁሉ ሰበሰበ፤ ባኦስ ይሠራበት የነበረውን የራማን ድንጋይና እንጨት ወሰደ፤ እርሱም ገባዖንንና መሴፋን ሠራበት። 7 በዚያን ጊዜም ነቢዩ አናኒ ወደ ይሁዳ ንጉሥ ወደ አሳ መጥቶ እንዲህ አለው፥ “በሶርያ ንጉሥ ታምነሃልና፥ በአምላክህም በእግዚአብሔር አልታመንህምና ስለዚህ የሶርያ ንጉሥ ጭፍራ ከእጆችህ አምልጠዋል። 8 ኢትዮጵያውያንና የልብያ ሰዎች እጅግ ብዙ ሰረገሎችና ፈረሰኞች የነበሩአቸው እጅግ ታላቅ ጭፍራ አልነበሩምን? በእግዚአብሔር ስለ ታመንህ በእጅህ አሳልፎ ሰጣቸው። 9 እግዚአብሔር ልቡ በእርሱ ዘንድ ፍጹም የሆነውን ያጸና ዘንድ ዐይኖቹ በምድር ሁሉ ይመለከታሉና። አሁንም ባለማወቅህ በድለሃል፤ ስለዚህም ከዛሬ ጀምሮ ጦርነት ይሆንብሃል።” 10 አሳም በነቢዩ በአናኒ ላይ ተቈጣ፤ ስለዚህም ነገር ተቈጥቶአልና በግዞት አኖረው፤ በዚያን ጊዜም አሳ ከሕዝቡ አያሌ ሰዎችን አስጨነቀ። 11 የአሳም የፊተኛውና የኋለኛው ነገር፥ እነሆ፥ በይሁዳና በእስራኤል ነገሥታት የታሪክ መጽሐፍ ተጽፎአል። 12 አሳም በነገሠ በሠላሳ ዘጠነኛው ዓመት እግሩን ታመመ፤ ደዌውም ጸናበት፤ ነገር ግን በሕማሙ ጊዜ ባለ መድኀኒቶችን እንጂ እግዚአብሔርን አልፈለገም። 13 አሳም ከአባቶቹ ጋር አንቀላፋ፤ በነገሠም በአርባ አንደኛው ዓመት ሞተ። 14 ለእርሱም ለራሱ በሠራው መቃብር በዳዊት ከተማ ቀበሩት፤ በቀማሚ ብልሃት የተሰናዳ ልዩ ልዩ መልካም ሽቱ በተሞላ አልጋ ላይም አኖሩት፤ እጅግም ታላቅ የሆነ የቀብር ሥርዐት አደረጉለት። |