1 ዜና መዋዕል 5 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የሮቤል ትውልድ 1 የእስራኤልም በኵር የሮቤል ልጆች እነዚህ ናቸው። እርሱ የበኵር ልጅ ነበረ፤ ነገር ግን ወደ አባቱ ምንጣፍ ስለ ወጣ አባቱ እስራኤል በረከቱን ለልጁ ለዮሴፍ ሰጠ፤ ብኵርናም አልተቈጠረለትም። 2 ይሁዳም በወንድሞቹ መካከል በረታ፥ አለቃም ከእርሱ ሆነ፤ በረከት ግን ለዮሴፍ ነበረ። 3 የእስራኤል በኵር የሮቤል ልጆች፤ ሄኖኅ፥ ፍሎስ፥ አስሮን፥ ከርሚ ነበሩ። 4 የኢዩኤል ልጆች፤ ልጁ ሰማያ፥ ልጁ ጎግ፥ ልጁ ሰሜኢ፤ 5 ልጁ ሚካ፥ ልጁ ሬካ፥ ልጁ ቤኤል፥ 6 የአሦር ንጉሥ ቴልጌልቴልፌልሶር የማረከው ልጁ ብኤራ፤ እርሱ የሮቤል ነገድ አለቃ ነበረ። 7 ወንድሞቹ በየወገናቸው የትውልዶቻቸው መዝገብ በተቈጠረ ጊዜ፥ አለቆቻቸው ኢዩኤልና ዘካርያስ ነበሩ። 8 እስከ ናባውና እስከ በኣልሜዎን ድረስ በአሮዔር የተቀመጠው የኢዩኤል ልጅ የሰማዕ ልጅ የዖዛዝ ልጅ ቤላ፤ 9 በገለዓድ ምድር እንስሶቻቸው በዝተው ነበርና በምሥራቅ በኩል ከኤፍራጥስ ወንዝ ጀምሮ እስከ ምድረ በዳው መግቢያ ድረስ ተቀመጠ። 10 በሳኦልም ዘመን ከስደተኞች ጋር ተዋጉ፥ እነርሱም በእጃቸው ተመትተው ወደቁ፤ በገለዓድ ምሥራቅ በኩል ባለው ሀገር ሁሉ በድንኳኖቻቸው ተቀመጡ። የጋድ ትውልድ 11 የጋድም ልጆች በባሳን ምድር እስከ ሰልካ ድረስ በአፋዛዣቸው ተቀመጡ። 12 በኵሩ ኢዩኤል፥ ሁለተኛው ሳፋም፥ ጸሓፊው ያናይን፥ ሳፋጥም በባሳን ተቀመጡ። 13 የአባቶቻቸው ቤቶች ወንድሞች ሚካኤል፥ ሜሱላም፥ ሳባ፥ ዮራይ፥ ያካን፥ ዙኢ፥ ኦቤድ እነዚህ ሰባት ነበሩ። 14 እነዚህም የቡዝ ልጅ የዮዳይ ልጅ የኢዮሳይ ልጅ የሚካኤል ልጅ የገለዓድ ልጅ የኤዳይ ልጅ የዑሪ ልጅ የአቢካኤል ልጆች ነበሩ። 15 የአባቶቻቸውም ቤቶች አለቃ የጎኔ ልጅ የአብዲኤል ልጅ ወንድም ነበር። 16 በገለዓድም ምድር በባሳን በመንደሮቹም በሳሮንም መሰማርያዎች ሁሉ እስከ ዳርቻቸው ድረስ ተቀምጠው ነበር። 17 እነዚህ ሁሉ በትውልዶቻቸው በይሁዳ ንጉሥ በኢዮአታም ዘመንና በእስራኤል ንጉሥ በኢዮርብዓም ዘመን ተቈጠሩ። የጋድና የምናሴ ነገድ እኩሌታ ትውልድ 18 የሮቤልና የጋድ ልጆች የምናሴም ነገድ እኩሌታ፥ ጽኑዓን ጋሻና ሰይፍ የሚይዙ፥ ቀስተኞችም፥ ሰልፍ የሚያውቁ ሰልፈኞችም፥ አርባ አራት ሺህ ሰባት መቶ ስድሳ ነበሩ። 19 ከአጋራውያንና ከኢጣርዮን ከናፋስዮንና ከናዳብዮን ጋር ተዋጉ። 20 በሚዋጉበትም ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጮኸዋልና በእርሱም ታምነዋልና አዳናቸው፤ በላያቸውም በረቱባቸው፥ አጋራውያንና ከእነርሱ ጋር የነበሩትም ሁሉ በእጃቸው ተሰጡ። 21 ከከብቶቻቸውም አምሳ ሺህ ግመሎች፥ ሁለት መቶ አምሳ ሺህም በጎች፥ ሁለት ሺህም አህዮች፥ ከሰዎችም መቶ ሺህ ማረኩ። 22 ሰልፉ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነበረና ብዙ ሰዎች ተገድለው ወደቁ፤ እስከ ምርኮም ዘመን ድረስ በስፍራቸው ተቀመጡ። 23 የምናሴም የነገድ እኩሌታ ልጆች፤ ከባሳን ጀምሮ እስከ በኣልአርሞንና እስከ ሳኔር እስከ አርሞንኤም ተራራ እስከ ሊባኖስ ድረስ ተቀመጡ፤ እነርሱም በዙ። 24 የአባቶቻቸውም ቤቶች አለቆች እነዚህ ነበሩ፤ ዔፌር፥ ይስዔ፥ ኤሊኤል፥ ዓዝርኤል፥ ኢይርምያ፥ ሆዳይዋ፥ ኢየድኤል፤ እነርሱ ጽኑዓን ኀያላን የታወቁ ሰዎች የአባቶቻቸውም ቤቶች አለቆች ነበሩ። 25 የአባቶቻቸውንም አምላክ በደሉ፤ እግዚአብሔርም ከፊታቸው ባጠፋቸው በምድሩ አሕዛብ አማልክት አመነዘሩ። 26 የእስራኤልም አምላክ የአሦርን ንጉሥ የፋሎክን መንፈስ፥ የአሦርንም ንጉሥ የቴልጌልቴልፌልሶርን መንፈስ አስነሣ፤ የሮቤልንና የጋድን ልጆች የምናሴንም ነገድ እኩሌታ አፈለሰ፥ እስከ ዛሬም ወዳሉበት ወደ አላሔና ወደ ኦቦር፥ ወደ ሃራንና ወደ ጎዛን ወንዝ አመጣቸው። |