ዘፍጥረት 11 - አዲሱ መደበኛ ትርጒምየባቤል ግንብ 1 በዚያ ጊዜ ሰዎች ሁሉ የሚናገሩትና የሚግባቡበት ቋንቋ አንድ ብቻ ነበር። 2 ሰዎቹም ምሥራቁን ይዘው ሲጓዙ፣ በሰናዖር አንድ ሜዳ አግኝተው በዚያ ሰፈሩ። 3 እነርሱም እርስ በርሳቸው፣ “ኑ፤ ጡብ እንሥራ፤ እስኪበቃውም በእሳት እንተኵሰው” ተባባሉ። በድንጋይ ፈንታ ጡብ፣ ለማያያዣም ቅጥራን ተጠቀሙ። 4 ከዚያም “ለስማችን መጠሪያ እንዲሆንና በምድር ላይ እንዳንበተን፣ ኑ፤ ከተማ፣ ሰማይ የሚደርስ ግንብም ለራሳችን እንሥራ” አሉ። 5 እግዚአብሔር ግን ሰዎቹ ይሠሩ የነበሩትን ከተማና ግንብ ለማየት ወረደ። 6 እግዚአብሔርም እንዲህ አለ፤ “እንዲህ እንደ አንድ ሕዝብ አንድ ቋንቋ በመናገር ይህን ማድረግ ከጀመሩ፣ ከእንግዲህ ያቀዱትን ሁሉ ማከናወን አያዳግታቸውም። 7 ኑ እንውረድ፤ እርስ በርሳቸውም እንዳይግባቡ ቋንቋቸውን እንደበላልቀው።” 8 ስለዚህ እግዚአብሔር በምድር ሁሉ ላይ በታተናቸው፤ ከተማዋንም መሥራት አቆሙ። 9 እግዚአብሔር በዚያ የመላውን ዓለም ቋንቋ ስለ ደበላለቀ የከተማዪቱ ስም ባቤል ተባለ። ከዚያም እግዚአብሔር ሰዎቹን በምድር ሁሉ በተናቸው። ከሴም እስከ አብራም 11፥10-27 ተጓ ምብ – ዘፍ 10፥21-32 ፤ 1ዜና 1፥17-27 10 የሴም ትውልድ ይህ ነው፦ ሁለት ዓመት ከጥፋት ውሃ በኋላ ሴም በ100 ዓመቱ አርፋክስድን ወለደ። 11 ሴም፣ አርፋክስድን ከወለደ በኋላ 500 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 12 አርፋክስድ በ35 ዓመቱ ሳላን ወለደ፤ 13 ሳላን ከወለደ በኋላ አርፋክስድ 403 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶችን ወለደ። 14 ሳላ በ30 ዓመቱ ዔቦርን ወለደ፤ 15 ዔቦርን ከወለደ በኋላ ሳላ 403 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 16 ዔቦር በ34 ዓመቱ ፋሌቅን ወለደ፤ 17 ፋሌቅን ከወለደ በኋላ ዔቦር 430 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 18 ፋሌቅ በ30 ዓመቱ ራግውን ወለደ፤ 19 ራግውን ከወለደ በኋላ ፋሌቅ 209 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 20 ራግው በ32 ዓመቱ ሴሮሕን ወለደ፤ 21 ሴሮሕን ከወለደ በኋላ ራግው 207 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 22 ሴሮሕ በ30 ዓመቱ ናኮርን ወለደ፤ 23 ናኮርን ከወለደ በኋላ ሴሮሕ 200 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 24 ናኮር በ29 ዓመቱ ታራን ወለደ፤ 25 ታራን ከወለደ በኋላ ናኮር 119 ዓመት ኖረ፤ ሌሎች ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። 26 ታራ 70 ዓመት ከሆነው በኋላ አብራምን፣ ናኮርንና ሐራንን ወለደ። 27 የታራ ትውልድ ይህ ነው። ታራ፣ አብራምን ናኮርንና ሐራንን ወለደ፤ ሐራንም ሎጥን ወለደ። 28 ሐራን፣ አባቱ ታራ ገና በሕይወት እንዳለ በከለዳውያን ምድር በምትገኘው በተወለደባት ከተማ በዑር ሞተ። 29 አብራምና ናኮር ሁለቱም ሚስት አገቡ፤ የአብራም ሚስት ሦራ ስትባል፣ የናኮር ሚስት ደግሞ ሚልካ ትባል ነበር፤ ሚልካም የሐራን ልጅ ናት፤ ሐራንም የሚልካና የዮስካ አባት ነበረ። 30 ሦራ መካን ነበረች፤ ልጅ አልነበራትም። 31 ታራ ልጁን አብራምን፣ ሐራን የወለደውን የልጅ ልጁን ሎጥን እንዲሁም የአብራምን ሚስት ምራቱን ሦራን ይዞ ወደ ከነዓን ለመሄድ በከለዳውያን ምድር ከምትገኘው ከዑር ዐብረው ወጡ፤ ነገር ግን ካራን በደረሱ ጊዜ በዚያ ተቀመጡ። 32 ታራ 205 ዓመት ኖሮ በካራን ሞተ። |
መጽሐፍ ቅዱስ፣ አዲሱ መደበኛ ትርጕም™
የቅጂ መብት © 2001, 2024 በBiblica, Inc.
በፈቃድ የሚወሰድ። በዓለም ዐቀፍ ባለቤትነቱ።
The Holy Bible, New Amharic Standard Version™
Copyright © 2001, 2024 by Biblica, Inc.
Used with permission. All rights reserved worldwide.
Biblica, Inc.