ሕዝቅኤል 35 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)ፍርድ በሴይር ተራራ ላይ 1 የጌታ ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦ 2 የሰው ልጅ ሆይ፥ ፊትህን ወደ ሴይር ተራራ አድርግ፥ ትንቢትም ተናገርበት፥ 3 እንዲህም በለው፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የሴይር ተራራ ሆይ፥ እነሆ በአንተ ላይ ነኝ፥ እጄን እዘረጋብሃለሁ ባድማና ውድማም አደርግሃለሁ። 4 ከተሞችህን ፍርስራሽ አደርጋቸዋለሁ፥ አንተም ባድማ ትሆናለህ፥ እኔም ጌታ እንደሆንሁ ታውቃለህ። 5 የዘለዓለም ጥል ስላለህ በመጨረሻው የፍርዳቸው ጊዜ፥ በመከራቸው ጊዜ የእስራኤልን ልጆች በሰይፍ እጅ ጥለሃቸዋልና፥ 6 ስለዚህ እኔ ሕያው ነኝና ይላል ጌታ እግዚአብሔር፥ ለደም አሳልፌ እሰጥሃለሁ ደምም ያሳድድሃል፥ ደምን ስላልጠላህ ደም ያሳድድሃል። 7 የሴይርን ተራራ ውድማና ባድማ አደርገዋለሁ፥ የሚሄደውንና የሚመለሰውንም ከእርሱ አጠፋለሁ። 8 ተራሮቹንም በተገደሉት ሰዎች እሞላለሁ፤ በኮረብቶችህ፥ በሸለቆዎችህና በውሃ መውረጃዎችህ ሁሉ ላይ በሰይፍ የተገደሉት ይወድቃሉ። 9 ለዘለዓለም ባድማ አደርግሃለሁ፥ ከተሞችህም ሰው አይኖርባቸውም፥ እኔም ጌታ እንደሆንሁ ታውቃላችሁ። 10 ጌታ በዚያ ሳለ፥ አንተ ግን፦ “እነዚህ ሁለቱ ሕዝቦችና እነዚህ ሁለቱ አገሮች ለእኔ ይሆናሉ እኛም እንወርሳቸዋለን” ብለሃልና፥ 11 ስለዚህ እኔ ሕያው ነኝና ይላል ጌታ እግዚአብሔር፥ እነርሱን ጠልተህ እንዳደረግኸው እንደ ቁጣህና እንደ ቅናትህ መጠን አደርጋለሁ፤ በፈረድሁብህም ጊዜ በእነርሱ መካከል ማንነቴን አስታውቃለሁ። 12 በእስራኤል ተራሮች ላይ “ፈርሰዋል እንድንበላቸው ለእኛ ተሰጥተዋል” ብለህ የተናገርኸውን ስድብ ሁሉ እኔ ጌታ እንደ ሰማሁት ታውቃለህ። 13 በአፋችሁ ታበያችሁብኝ፥ ንግግራችሁንም በእኔ ላይ አበዛችሁ፤ እኔም ሰምቼዋለሁ። 14 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ምድር ሁሉ ስትደሰት አንተን ባድማ አደርግሃለሁ። 15 የእስራኤል ቤት ርስት ባድማ በመሆኑ እንደተደሰትህ፥ እንዲሁ አደርግብሃለሁ፤ የሴይር ተራራ ሆይ፥ አንተ፥ ኤዶም ሁሉና ሁለንተናዋ ባድማ ትሆናላችሁ፤ እኔም ጌታ እንደሆንሁ ያውቃሉ። |