Biblia Todo Logo
A Bíblia On-line

- Anúncios -


ሕዝቅኤል 28 - መጽሐፍ ቅዱስ - (ካቶሊካዊ እትም - ኤማሁስ)


በጢሮስ ንጉሥ ላይ የተነገረ ሙሾ

1 የጌታ ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦

2 የሰው ልጅ ሆይ፥ የጢሮስን ገዥ እንዲህ በለው፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ልብህ ኰርቶአል አንተም እንዲህ ብለሃል፦ እኔ አምላክ ነኝ፥ በእግዚአብሔር ወንበር በባሕር ልብ ተቀምጫለሁ፤ ነገር ግን ልብህን እንደ እግዚአብሔር ልብ ብታደርግም አንተ ሰው ነህ እንጂ አምላክ አይደለህም።

3 እነሆ፥ አንተ ከዳንኤል ይልቅ ጥበበኛ ነህ፥ ከአንተ የተሰወረ ምሥጢር የለም።

4 በጥበብህና በማስተዋልህ ሀብትን ለራስህ አግኝተሃል፥ ወርቅና ብርም በግምጃ ቤትህ ውስጥ ሰብስበሃል።

5 በጥበብህ ብዛትና በንግድህ ሀብትህን ጨምረሃል፥ በሀብትህም ልብህ ኰርቶአል።

6 ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ልብህን እንደ እግዚአብሔር ልብ አድርገሃልና፥

7 ስለዚህ እነሆ ባዕዳንን፥ ጨካኞች መንግሥታትን አመጣብሃለሁ፤ በጥበብህ ውበት ላይ ሰይፋቸውን ይመዝዛሉ፥ ድምቀትህን ያረክሳሉ።

8 ወደ ጉድጓድ ያወርዱሃል፤ በባሕር ልብ ተገድለው በሞቱበት ሞት ትሞታለህ።

9 በገዳይህ ፊትም፦ “እኔ አምላክ ነኝ” ትላለህን? ቢሆንም አንተ በገዳይህ እጅ ሰው ነህ እንጂ አምላክ አይደለህም።

10 በባዕዳን እጅ ያልተገረዙትን ሰዎች ሞት ትሞታለህ፤ እኔ ተናግሬአለሁና፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።


በጢሮስ ንጉሥ ላይ የወጣ ሙሾ

11 የጌታ ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦

12 የሰው ልጅ ሆይ፥ በጢሮስ ንጉሥ ላይ ሙሾ አሞሽተህ እንዲህ በለው፦ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ጥበብን የተሞላህ ውበትህም የተፈጸመ መደምደሚያ አንተ ነህ።

13 በእግዚአብሔር የአትክልት ቦታ በዔድን ነበርህ፤ የከበረ ድንጋይ ሁሉ ልብስህ ነበር፥ ያቁት፥ ቶጳዝዮን፥ አልማዝ፥ ቢረሌ፥ መረግድ፥ ኢያስጲድ፥ ሰንፔር፥ በሉር፥ የሚያብረቀርቅ ዕንቁ፥ ወርቅ፥ ልብስህ ነበረ፤ የከበሮህና የእንቢልታህ ሥራ በአንተ ዘንድ ነበረ፤ በተፈጠርህበት ቀን ተዘጋጅተው ነበር።

14 አንተ ልትጋርድ የተቀባህ ኪሩብ ነበርህ፤ በተቀደሰው በእግዚአብሔር ተራራ ላይ አኖርሁህ፤ በእሳት ድንጋዮች መካከል ተመላለስህ።

15 ከተፈጠርህበት ቀን ጀምረህ በደል እስኪገኝብህ ድረስ በመንገድህ ፍጹም ነበርህ።

16 በንግድህ ብዛት ግፍ በውስጥህ ተሞላ ኃጢአትንም ሠራህ፤ ስለዚህ እንደ ርኩስ ነገር ከእግዚአብሔር ተራራ ጣልሁህ፤ የምትጋርድ ኪሩብ ሆይ፥ ከእሳት ድንጋዮች መካከል አጠፋሁህ።

17 በውበትህ ምክንያት ልብህ ኰርቶአል፤ ከክብርህ የተነሣ ጥበብህን አረከስህ፤ በምድር ላይ ጣልሁህ ያዩህም ዘንድ በነገሥታት ፊት ሰጠሁህ።

18 በበደልህ ብዛት በንግድህም ኃጢአት መቅደስህን አረከሰህ፤ ስለዚህ እሳትን ከውስጥህ አውጥቻለሁ እርሷም በልታሃለች፥ በሚያዩህም ሁሉ ፊት በምድር ላይ አመድ አድርጌሃለሁ።

19 በአሕዛብም ውስጥ የሚያውቁህ ሁሉ ይደነቁብሃል፤ አንተ ለድንጋጤ ሆነሃል፥ እስከ ዘለዓለምም አትገኝም።


በሲዶና ላይ የታወጀ አዋጅ

20 የጌታ ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ፦

21 የሰው ልጅ ሆይ፥ ፊትህን ወደ ሲዶና አቅንተህ ትንቢት ተናገርባት፥ እንዲህም በል፦

22 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ሲዶና ሆይ፥ እነሆ፥ በአንቺ ላይ ነኝ፥ በውስጥሽም እከብራለሁ፤ ፍርድንም ባደረግሁባት ጊዜ በተቀደስሁባትም ጊዜ እኔ ጌታ እንደሆንሁ ያውቃሉ።

23 ቸነፈርንም በእርሷ ላይ፥ ደምንም በጎዳናዋ እሰድዳለሁ፤ ከዙሪያዋ በላይዋ ባለ ሰይፍ የተወጉ በመካከልዋ ይወድቃሉ፤ እኔም ጌታ እንደሆንሁ ያውቃሉ።

24 ከእንግዲህም ወዲያ ለእስራኤል ቤት የሚወጋ እሾህ፥ በዙሪያቸውም ካሉ ከናቋቸው ሁሉ የሚያቆስል ኩርንችት አይሆንም፤ እኔም ጌታ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ያውቃሉ።


የእስራኤል መባረክ

25 ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ የእስራኤልን ቤት ከተበተኑባቸው አሕዛብ ዘንድ በሰበሰብሁ ጊዜ፥ በአሕዛብም ፊት በተቀደስሁባቸው ጊዜ፥ ለባርያዬ ለያዕቆብ በሰጠኋት ምድራቸው ይቀመጣሉ።

26 ተዘልለውም ይቀመጡባታል፤ ቤቶችንም ይሠራሉ ወይኑንም ይተክላሉ በዙሪያቸውም ባሉ በሚንቋቸው ሁሉ ላይ ፍርድን ባደረግሁ ጊዜ ተዘልለው ይቀመጣሉ፤ እኔም ጌታ አምላካቸው እንደሆንሁ ያውቃሉ።

Siga-nos em:



Anúncios