Este libro no es inspirado por Dios y no forma parte del canon cristiano ni del Tanaj judío. Se muestra solo con fines históricos y de estudio. Ver explicación completa መጽሐፈ ጥበብ 13 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)የጣዖት አምልኮ ከንቱነት 1 እግዚአብሔርን የማወቅ ጕድለት በልቡናቸው ያለባቸው ሰዎች ሁሉ በእውነት ከንቱ ናቸውና፥ በሚታዩ መልካም ነገሮች ያለውን ያውቁ ዘንድ ተሳናቸው፥ ሥራውንም እያዩ ሠሪውን አላወቁትም። 2 ነገር ግን እሳትንና ፈጥኖ የሚነፍሰውን ነፋስ፥ ወይም የከዋክብትን ዙረት፥ ወይም የውኃውን ሞገድ፥ ወይም የሰማይ ብርሃናትን ዓለሙን የሚያስተዳድሩ አማልክት አስመሰሏቸው። 3 በመልካቸው ውበት ደስ ባላቸው ጊዜ እነዚህን ፍጥረታት አማልክት ካደረጓቸው፥ ውበትን የፈጠረ እርሱ ይህን ፍጥረት ፈጥሯልና የእነዚህ ጌታ ፈጽሞ እንደሚበልጥ ይወቁ። 4 ከኀይላቸውና ከሥራቸው የተነሣ ከተደነቁስ የፈጠራቸው እርሱ ፈጽሞ ኀያል እንደ ሆነ ያስተውሉ። 5 ፍጡራን የፍጥረታትን ውበት ታላቅነት አይተው የፍጥረታትን ፈጣሪ በእርሱ መስለውታል። 6 ነገር ግን ከዚህ ጋራ ዳግመኛ አምላክን እየፈለጉት፥ ያገኙትም ዘንድ እየወደዱ ቢሳሳቱ፥ በእነርሱ ላይ የሚኖረው ነቀፋ ጥቂት አይደለም። 7 ወደ ሥራው ተመልሰው በፈለጉት ነበርና፥ እነርሱ ግን በማየት አበቁ፥ የሚታዩት መልካሞች ናቸውና። 8 ዳግመኛም ምክንያታቸው ብዙ ነው። 9 ዓለምን መረዳት እስኪገባቸው ድረስ ይመለከቱ ዘንድ ይህን ያህል ከተቻላቸው የእነዚህን ጌታ ፈጥነው ያገኙት ዘንድ እንዴት አልቻሉም? 10 ከወርቅና ከብር በጥበብ የተሠሩ የሰው እጅ ሥራዎችን፥ የእንስሳ ምሳሌን፥ ወይም የማይጠቅም የጥንት የእጅ ሥራ ድንጋይን አማልክት ብለው የሚጠሩ እነዚህ ጐስቋሎች ናቸው፥ ተስፋቸውም በሞቱ ነገሮች ላይ ነው። 11 የሚታየውንና የሚወዛወዘውን እንጨት የሚጠርብ ጠራቢ ቢኖር መልካም ሆኖ የበቀለውን እንጨት ይቈርጣል፥ ቅርፊቱን ሁሉ በጥበብ ይጠርባል፤ መልካም አድርጎም ይሠራዋል፥ ለኑሮ አገልግሎትም የሚጠቅም ዕቃ አድርጎ ይሠራዋል። 12 ምግቡንም ለማዘጋጀት የሥራውን ጠረባ ከፈጸመ በኋላ ይጠግባል። 13 ዳግመኛም ለምንም ከማይጠቅም እንጨት የተረፈ ጕማጁን፥ ጕጣሙንና ጫፉ ሁሉ የጠመመውን እንጨት ወስዶ ሥራውን በማስተንተን ይጠርበዋል፥ ከዚህም በኋላ በቦዘነበት ቀን በሰው መልክ መስሎ ይቀርፀዋል። 14 ወይም ከንቱ በሚሆን በእንስሳ ምስል ይሠራዋል፥ በቀይ ቀለምም ይቀባዋል፤ በጣቱም ቀለም አግብቶ ቀይ ያደርገዋል። ያለበትንም ጕድለት ይሞላል። 15 ለእርሱም የሚገባ የውቅር ቤት ይሠራል፤ በሠራለት ቦታም ያኖረዋል፥ ከግድግዳውም አስጠግቶ በብረት ይቸነክረዋል። 16 ምስል ነውና፥ የሚረዳውንም ይፈልጋልና ራሱን መርዳት እንደማይችል ዐውቆ እንዳይወድቅበት ይጠነቀቃል። 17 ከዚህም በኋላ ስለ ገንዘቡና ስለ ሚስቱ፥ ስለ ልጆቹም ወደ እርሱ ይለምናል፤ ነፍስ ከሌለው ከጣዖቱ ጋርም ሲነጋገር አያፍርም። 18 ስለ ፈውስ ወደ በሽተኛው ይለምናል፥ ስለ ሕይወትም መዋቲውን ይለምናል፥ ስለ ርዳታም መርዳት ወደማይችለው ደካማ ይማልዳል። 19 ስለ መንገድም ነገር ይንቀሳቀስ ዘንድ ወደማይቻለውና አንዲት ርምጃን ወደማይራመደው ይለምናል። ስለ ብልጽግናና ስለ ሥራም፥ ስለ ማግኘትም፥ የእጅን ሥራም ስለ ማቅናት እጆቹ ምንም ወደማይሠሩ ይለምናል፥ ኀይልንና ሥራ ማፍጠንንም ይሰጠው ዘንድ ምንም ኀይል ከሌለው ከእርሱ ይፈልጋል። |