Este libro no es inspirado por Dios y no forma parte del canon cristiano ni del Tanaj judío. Se muestra solo con fines históricos y de estudio. Ver explicación completa መጽሐፈ ሲራክ 39 - የአማርኛ መጽሐፍ ቅዱስ (ሰማንያ አሃዱ)1 ጥበብስ በቀደሙ ሰዎች ሁሉ ዘንድ ተመረመረች። 2 በሃይማኖት ስማቸውን ላስጠሩ ሰዎች ትንቢትን ታስተምራለች፤ ወደ ነቢያትም ምሳሌ ታገባለች። 3 የተሰወረውንም ምሳሌ ትመረምራለች፤ ምሳሌውንም ወደ መተርጐም ትመልሳለች። 4 በመኳንንትም መካከል ትጠቅማለች፤ በአለቆችም መካከል ትታያለች፤ ልዩ ወደ ሆኑ ወደ አሕዛብም ሀገር ትገባለች፤ 5 ሰዎችን በበጎም፥ በክፉም ትፈትናቸዋለችና፥ ወደ ፈጣሪው ወደ እግዚአብሔር ይሄድ ዘንድ፥ በልዑልም ፊት ይጸልይ ዘንድ ልቡን ይመልሳል፤ አፉንም ይከፍታል፤ ይለምናልም፤ ስለ ኀጢአቱም ይናዘዛል። 6 ነገር ግን ገናና የሆነው እግዚአብሔር ከፈቀደ፥ የጥበብንም መንፈስ ካሳደረበት፥ እርሱ የጥበቡን ነገር ያፈልቃል፤ በጸሎቱም ለእግዚአብሔር ይገዛል። 7 እርሱም ጥበብንና ምክርን ይገልጥለታል፤ የተሰወረውንም ያውቅ ዘንድ ያሳስበዋል። 8 እርሱም የትምህርቱን ጥበብ ያሳያል፤ በእግዚአብሔር የኪዳን ሕግም ይመካል። 9 ስለ ጥበቡም ብዙ ሰዎች ያመሰግኑታል፤ ለዘለዓለሙም አይደመሰስም፤ ስም አጠራሩም አይጠፋም፤ ስሙም ለልጅ ልጅ ጸንቶ ይኖራል። 10 አሕዛብም ጥበቡን ይናገራሉ፤ በሸንጎ መካከልም ያመሰግኑታል። 11 ከሺህ ልጅ ስምን ማስጠራት ይሻላል፤ ከሞተም በኋላ ሥራው ጸንቶ ይኖራል። የምስጋና መዝሙር 12 ዳግመኛም አስቤ እናገራለሁ፤ እንደ ሙሉ ጨረቃ ሙሉ ነኝና። 13 የጻድቃን ልጆች ስሙኝ፤ ለምልሙ፤ ታደሱ፤ አበባ በምድረ በዳ ጠል እንደሚያብብ አብቡ። 14 እንደ ሊባኖስ መዓዛ መዓዛችሁ ይጣፍጥ፤ አበባችሁን እንደ ጽጌረዳ አብቅሉ ፤ መዓዛችሁንም አጣፍጡ፤ መዝሙርን ዘምሩ፤ በሥራውም ሁሉ እግዚአብሔርን አመስግኑት። 15 ስሙን አግንኑት፤ በአንድ ሺህ መዝሙርና በመሰንቆ ስሙን አግንኑት በምታመሰግኑትም ጊዜ እንዲህ በሉ። 16 “የእግዚአብሔር ሥራው ገናና ነው። እጅግም ያማረ ነው፤ ሥርዐቱም ሁሉ በየጊዜው ነው።” 17 “ይህ ለምንድን ነው? ያስ ለምንድን ነው?” ማለት አይገባም፤ ሁሉም በጊዜው ይፈቀዳል፤ ውኃውንም በቃሉ እንደ ግድግዳ አጸናው፤ በአፉ ቃልም እንደ ኵሬ ውኃ፤ 18 በትእዛዙም ሁሉ የተወደደ ነው፤ መድኀኒትነቱንም የሚያጐድል የለም። 19 የሰው ሁሉ ሥራ በፊቱ ነው፤ ከዐይኖቹም ፊት መሰወር የሚችል የለም። 20 ዓለም ሳይፈጠር እስከ ዘለዓለም ድረስ ሁሉን ዐወቀ፤ በፊቱም ምንም ልዩ ፍጥረት የለም። 21 ሁሉም ለመፍቅዳቸው ተፈጥሯልና “ይህ ለምንድን ነው? ያስ ለምንድን ነው?” የሚል የለም። 22 በረከቱም እንደ ፈሳሽ ውኃ መላች፤ እንደ ጎርፍ ውኃም ምድርን አረካቻት፤ 23 እንደዚሁ ቍጣው አሕዛብን ከፈለቻቸው። 24 የጻድቅ መንገዱ የቀና ነው፤ የኃጥእ መንገድ ግን ዕንቅፋት ነው፤ ውኃውንም የሚለውጠው፥ ጨውም የሚያደርገው እርሱ ነው። 25 በጎ ነገር ከጥንት ጀምሮ ለበጎ ሰዎች ተፈጠረች፤ እንደዚሁ ክፉ ነገርም ለኃጢአተኞች ተፈጠረች። 26 የሰው የመፍቅዱ ሁሉ መጀመሪያ፥ ውኃ፥ እሳት፥ ብረት፥ ጨው፥ እህል፥ ስንዴ፥ ማር፥ ወተት፥ ወይን፥ ዘይትና ልብስ ነው። 27 ይህ ሁሉ ለጻድቃን ሰዎች በረከታቸው ነው፤ እንደዚሁም ሁሉ በኀጢአተኞች ሰዎች ወደ ክፉ ይመለስባቸዋል። 28 ለበቀል የተፈጠረች መንፈስ አለች፤ በጥፋታቸው መቅሠፍታቸውን ያበዟታል፤ በዘመናቸው ኀይላቸው ይደክማል፤ የፈጣሪያቸው መቅሠፍትም ይመጣባቸዋል። 29 እሳት፥ በረድ፥ ረኃብና ቸነፈር ይህ ሁሉ ለበቀል ተፈጠረ። 30 የምድር አራዊት ጥርስ ጊንጥና እፉኝት፥ ጦርም ኀጢአተኞችን ታጠፋቸው ዘንድ ተፈጠረች። 31 እርሱ ግን በይቅርታው ደስ ያሰኛል፤ የዓለምንም መፍቅድ ያዘጋጃል። ሁሉም ጊዜው ከደረሰ ከዕድሜው አያልፍም። 32 ስለዚህ ነገር ከጥንት ጀምሮ ሁሉም ተዘጋጀ፤ ይህንም አስቤ በመጽሐፍ ጻፍሁት። 33 የእግዚአብሔር ሥራው ሁሉ ያማረ ነውና፤ ለሰውም በየጊዜው መፍቅዱን ይሰጣል። 34 “ይህን ክፉ ፈጠርህ፤ ያንም አሳመርህ” የሚለው የለም። ሁሉን ቀኑ ይገልጠዋልና። 35 አሁንም በፍጹም ልቡናችሁ፤ በፍጹምም አንደበታችሁ እግዚአብሔርን አመስግኑት፤ ሁልጊዜም ለስሙ ምስጋና አቅርቡ። |